የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

በዞኑ በበጋ መስኖ ከ41 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት ይለማል

Oct 11, 2025

IDOPRESS

🔇Unmute

ደብረ ማርቆስ ፤ መስከረም 30/2018 (ኢዜአ)፡-በምስራቅ ጎጃም ዞን በመጪው በጋ ከ41 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በመስኖ ለማልማት መታቀዱን የዞኑ ግብርና መምሪያ ገለጸ።

በመምሪያው የመስኖ ልማት ቡድን መሪ አቶ ሃብታሙ መሃመድ ለኢዜአ እንደገለጹት የምግብ ሉዓላዊነትን በዞን ደረጃ ለማረጋገጥ መስኖን በስፋት መጠቀም እንደሚገባ አቅጣጫ በማስቀመጥ እየተሰራ ነው።

በዚህም በመጪው የበጋ ወቅት ከ41 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በመስኖ በማልማት 4 ነጥብ 4 ሚሊዮን ኩንታል ምርት ለመሰብሰብ ታቅዶ ወደ ስራ መገባቱን ገልጸዋል።

ከ120 ሺህ በላይ አርሶ አደሮችን በማሳተፍ ከሚለማው መሬት ውስጥም ከ21 ሺህ ሄክታር በላይ የሚሆነው በበጋ ስንዴ የሚሸፈን መሆኑን አስረድተዋል።

የመስኖ ልማቱን ምርታማነት ለማሳደግም ከ100 ሺህ ኩንታል በላይ የፋብሪካ ማዳበሪያና ከ347 ሺህ ኩንታል በላይ ኮምፖስት እንዲሁም ምርጥ ዘር ጥቅም ላይ ለማዋል እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

የሞተር ፓምፖችን የማቅረብ፣ አርሶ አደሮችንና ባለሙያዎችን የማሰልጠን፣ የውሃ ማቆርና የካናል ጠረጋ ተግባራት በቅድመ ዝግጅት የሚሰሩ ስራዎች መጠናቀቃቸውን ተናግረዋል።

በዞኑ የጎዛምን ወረዳ የደሳ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ተዋቸው ሆደሞኝ፤ በዘንድሮው በጋ በመስኖ ልማት በንቃት ለመሳተፍ አሁን ላይ ቀድሞ የደረሰውን የገብስ ሰብል በመሰብሰብ ላይ ነኝ ብለዋል ።

በጥቅምት አጋማሽ መስኖ በመጠቀም ከሩብ ሄክታር በላይ ማሳቸውን በጓሮ አትክልት በማልማት በበጀት ዓመቱ ከ50 ሺህ ብር በላይ ተጨማሪ ገቢ ለማግኘት እየሰሩ መሆኑን አስረድተዋል።


ሌላው የዚሁ ወረዳ የብራጌ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር ልየው በለጠ በበኩላቸው በመስኖ ልማት በየዓመቱ በመሳተፍ ተጠቃሚ መሆናቸውን አውስተዋል።

በዘንድሮው በጋም ከአንድ ሄክታር በላይ መሬታቸውን የተለያዩ ሰብሎችን ለመዝራት መዘጋጀታቸውን ገልጸዋል።

በዞኑ ባለፈው ዓመት በተካሄደው የበጋ መስኖ ልማት ስራ ከ3 ነጥብ 7 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት በማግኘት ገበያ የማረጋጋት ስራ መሰራቱን ከዞኑ የተገኘው መረጃ ያመላክታል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.