የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

"ጀፎረ" ከገጠር ኮሪደር ልማት ጋር እንዲተሳሰር መደረጉ የአካባቢውን የቱሪስት መስህብነት እያሳደገው ነው

Nov 7, 2025

IDOPRESS

🔇Unmute

ወልቂጤ፤ ጥቅምት 27/2018(ኢዜአ)፦የጉራጌ ማህበረሰብ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ መከወኛ "ጀፎረ" ከገጠር ኮሪደር ልማት ጋር መተሳሰሩ የአካባቢውን የቱሪስት መስህብነት እያሳደገው መምጣቱን የጉራጌ ዞን አስተዳደር ገለጸ።

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢኒሼቲቭ የተጀመረው የገጠር ኮሪደር ልማት በስፋት ተግባራዊ ከሆነባቸው የሀገሪቱ አካባቢዎች የጉራጌ ዞን አንዱ ነው።

ልማቱ የዞኑን አርሶ አደር አኗኗር ከማዘመን ባለፈ ለዓመታት ባህሉ አድርጎ ሲጠቀምበት የቆየውን ''ጀፎረ''ን የቱሪስት መስህብ እንዲሆን እያስቻለ መሆኑ ተገልጿል፡፡

ጀፎረ የጉራጌ ማህበረሰብ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ እንቅስቃሴዎችን ከጥንት ጀምሮ የሚከውንበት ሲሆን ከኮሪደር ልማቱ ጋር ተሳስሮ እንዲለማ መደረጉ የቱሪስት መስህብነቱ ይበልጥ እንዲጨምር አድርጓል።


የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ ጀፎረን ከገጠር ኮሪደር ልማት ጋር አቀናጅቶ ለማልማት የተሰጠው ትኩረት ውጤት እያስገኘ መሆኑን ገልፀዋል።


ልማቱ አካባቢውን ውብና ይበልጥ ሳቢ ከማድረግ ባለፈ በተለያዩ የዞኑ አካባቢዎች የሀገር ውስጥና የውጭ ጎብኚዎች ቁጥር እየጨመረ እንዲመጣ ማድረጉን ጠቅሰው፣ በዚህም በአካባቢው በአገልግሎት ሰጭነት የተሰማሩ ተቋማት ገቢያቸው ማደጉን ተናግረዋል።

እንደ አቶ ላጫ ገለጻ የገጠር ኮሪደር ልማቱ የአርሶ አደሩን የአኗኗር ዘይቤ በመቀየር በኩልም የጎላ ሚና እየተጫወተ ነው።

በቀጣይም ማህበረሰብ አቀፍ የቱሪዝም ሀብት በማድረግ ለገቢ ምንጭነት ለማዋል ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል።

የዞኑ ባህልና ቱሪዝም መምሪያ ሃላፊ ወይዘሮ መሰረት አመርጋ በበኩላቸው፤ ጀፎረን ከገጠር ኮሪደር ልማት ጋር በማስተሳሰር የማልማትና የማስተዋወቅ ሥራዎች መከናወናቸውን ገልጸዋል።

ከገጠር ኮሪደር ልማት በተጨማሪ የአካባቢው ሰላምና የህዝቡ እንግዳ ተቀባይነት በየጊዜው የጎብኚዎች ቁጥር እንዲጨምር አስተዋጽኦ ማድረጉን ጠቅሰው፣ ይህን ወደ ማህበረሰብ አቀፍ ቱሪዝም ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን ተናግረዋል።


ለገጠር ኮሪደር ውጤታማነት የማህበረሰቡ ተሳትፎ የጎላ መሆኑንም ወይዘሮ መሰረት ጠቅሰዋል።

አስተያየታቸውን የሰጡት በዞኑ የእኖር ወረዳ ነዋሪ አቶ ትዕግስቱ ሃብቴ እና አርሶ አደር መሃሙድ ያሲን የገጠር ኮሪደር ልማት የአካባቢያቸውን ገጽታ መቀየሩ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ጎብኚዎች ወደአካባቢው እንዲመጡ እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።


ይህም በገጠር ኮሪደር ልማት ያላቸውን ተሳትፎ ለማሳደግ እንዳነሳሳቸው የገለጹት ነዋሪዎቹ፣ ልማቱ ከጀፎረ ጋር እንዲተሳሰር መደረጉ የጎብኚዎችን ቀልብ ይበልጥ ለመሳብ ማስቻሉን ተናግረዋል።


በተለይ ውብ የገጠር መንደሮች፣ በአካባቢው የሚከወኑ ማህበራዊ እንቅስቃሴዎች፣ መንደሮችን ተከትለው የተሰሩ ባህላዊ ቤቶች፣ የእንሰት፣ የአትክልትና ፍራፍሬ ልማቶች የጎብኚዎችን ቀልብ እንደሚስቡም አስረድተዋል።

ለቱሪስቶች መስህብ እየሆነ የመጣው የገጠር ኮሪደር ልማት ለአካባቢው ማህበረሰብም የገቢ ምንጭ እንዲሆን በትኩረት መስራት እንደሚገባም ነዋሪዎቹ ጠይቀዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.