የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ህይወት እና ጉዞ

ትውልዱ ከዓድዋ ድል የወረሰውን የጀግንነት እሴት የሀገርን ብሔራዊ ጥቅም በማስጠበቅ ሊተገብረው ይገባል

Mar 4, 2026

IDOPRESS

🔇Unmute

ገንዳውኃ፤ የካቲት 23/2018(ኢዜአ)፦ትውልዱ ከዓድዋ ድል የወረሰውን የጀግንነት እሴት የሀገርን ሉዓላዊነትና ብሔራዊ ጥቅም በማስጠበቅ ሊተገብረው እንደሚገባ ተመላከተ።

የዓድዋ ድል የመላው ጥቁር ሕዝቦች የነፃነት ምልክት ነው

የዓድዋ ድል 130ኛ ዓመት መታሰቢያ በምዕራብ ጎንደር ዞን ገንዳ ውሃ ከተማና በደብረ ማርቆስ ከተማ ''ከአኩሪ ታሪክ ወደ ብሩህ አድማስ'' በሚል መሪ ሀሳብ አባት አርበኞች፣ ከፍተኛ የመንግስት የሥራ ሃላፊዎችና ነዋሪዎች በተገኙበት ተከብሯል።

በገንዳ ውሃ ከተማ በተካሄደው ሥነ-ሥርዓት ላይ የተገኙት የምዕራብ ጎንደር ዞን ዋና አስተዳዳሪ እያሱ ይላቅ፣ የዓድዋ ድል በአባቶቻችን ቆራጥ ተጋድሎ፣ በደምና በአጥንት የታተመ የኢትዮጵያዊያን የአሸናፊነት አሻራ ነው ብለዋል።

ዓድዋ የትናንት ታሪክ ብቻ ሳይሆን የወቅቱና የቀጣይ መመሪያ መሆኑን ገልጸው፣ወጣቱ ትውልድ ይህን ታላቅ ታሪክ ሲያከብር እንደ አባቶቹ በአይበገሬነት መንፈስ ተግቶ መስራትና ብሔራዊ ጥቅምን ማስከበር አለበት ብለዋል።


ትውልዱ ከዓድዋ ድል የወረሰውን የጀግንነት እሴት የሀገር ሉዓላዊነትና ብሔራዊ ጥቅምን ለማስጠበቅ ሊያውለው እንደሚገባም አሳስበዋል።

የምዕራብ ጎንደር ዞን አባት አርበኞች ተጠሪ በቀለ ጀመረ በበኩላቸው፣ ዓድዋ የጥቁር ህዝቦችን የአሸናፊነትና መንፈስ የመለሰ ታላቅ ክስተት መሆኑን አስታውሰው፣ጀግኖች አባቶች ያቆሟትን ሀገር ለቀጣዩ ትውልድ ለማስተላለፍ የዛሬው ወጣት በቁርጠኝነት ሊሰራ ይገባል ብለዋል።

የበዓሉ ተሳታፊ ወጣት ኪሩቤል መንግስቴ፤ ወጣቱ የጥንታዊ አባቶች የጀግንነት ታሪክን ከማስታወስ ባለፈ የሀገርን የውስጥና የውጭ ችግሮች በመፍታት የራሱን አዲስ ታሪክ መስራት አለበት ብሏል።

በተመሳሳይ የደብረ ማርቆስ ከተማ አስተዳደር ከምስራቅ ጎጃም ዞን ጥንታዊ ኢትዮጵያ አርበኞች ማህበር ጋር በመተባበር 130ኛውን የዓድዋ ድል በዓል አክብሯል።

የምስራቅ ጎጃም ዞን የጥንታዊ ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማህበር ሊቀመንበር ነብዩ እስቅየል፤ ድሉ የተገኘው በመላው ኢትዮጵያውያን የአላማ ጽናትና አገር ወዳድነት መሆኑን ገልጸዋል።


የከተማዋ ተቀዳሚ ምክትል ከንቲባ ተሾመ ዋለ በበኩላቸው፤ ዓድዋ የሕብረ-ብሔራዊ አንድነታችን መገለጫና የጥቁር ህዝቦች የእኩልነት ማረጋገጫ ማህተም ነው ብለዋል።


የበዓሉ ታዳሚ መምህር የሻንበል ግዛቸው የዓድዋን እሴቶችና ያስገኘውን ነጻነትና እኩልነት ለተተኪው ትውልድ ማስተማር እንደሚገባ አስገንዝበዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.