የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ህይወት እና ጉዞ

አስተዳደሩ የህብረተሰቡን የመኖሪያ ቤት ችግር ለማቃለል ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ነው

Mar 4, 2026

IDOPRESS

🔇Unmute

አምቦ ፤ የካቲት 24/2018 (ኢዜአ)፦የአምቦ ከተማ አስተዳደር የህብረተሰቡን የመኖሪያ ቤት ችግር ለማቃለል ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ መሆኑን ገለጸ፡፡

በአምቦ ከተማ ያለውን የመኖሪያ ቤት ችግር ለማቃለል በማህበር ለተደራጁ 1 ሺህ 516 ነዋሪዎች የቤት መስሪያ ቦታ ተሰጥቷል።

ለከተማው ነዋሪዎች ዛሬ የቤት መስሪያ ቦታ የተሰጠው በከተማው ማዘጋጃ ቤት በተከናወነ እጣ የማውጣት መርሀግብር ነው።

በሸገር ከተማ የጤና አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል የተከናወኑ ተግባራት ውጤት እያመጡ ነው

የቦታ ርክክብ መርሀግብሩ ላይ የተገኙት የአምቦ ከተማ ከንቲባ ሃጫሉ ገመቹ እንደገለጹት፤ የቤት መስሪያ ቦታ የተሰጠው በከተማዋ ያለውን የመኖሪያ ቤት ፍላጎት ታሳቢ በማድረግ ነው።

የቤት መስሪያ ቦታ መሰጠቱ በነዋሪዎች ዘንድ ሲነሳ የነበረን ቅሬታ እንደሚያቃልል ገልጸው፣ በበጀት ዓመቱ የቤት መሰሪያ ቦታ ከተሰጣቸው ነዋሪዎች መካከል አብዛኞቹ የመንግስት ሠራተኞች ናቸው ብለዋል።

ነዋሪዎቹ በከተማዋ ማስተር ፕላን መሰረት ደረጃውን የጠበቀ ቤት መስራት እንደሚጠበቅባቸው ገልጸው፣ በቀጣይም የህብረተሰቡን የመኖሪያ ቤት ችግር ለማቃለል አስተዳደሩ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።


የአምቦ ከተማ መሬት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ መርጋ ወዳጆ በበኩላቸው፤ በወጣው ዕጣ መሰረት ለማህበራቱ የቦታ ርክክብ መደረጉን ገልጸዋል።

ዛሬ የቤት መስሪያ ቦታ የተሰጠው በ75 የቤት ማህበራት ለተደራጁ 1 ሺህ 516 ነዋሪዎች ሲሆን ነዋሪዎቹም በተለያዩ ማህበራት ተደራጅተው ከሦስት እስከ ሰባት ዓመት ሲጠባበቁ የቆዩ መሆናቸውን ተናግረዋል።

እንደ ኃላፊው ገለጻ ቦታው የተዘጋጀው በአምቦ ከተማ አዋሮ ቆራ ቀበሌ ሲሆን በእዚህም ለእያንዳንዱ ተጠቃሚ 140 ካሬ ሜትር ቦታ ተሰጥቷል።

ከዕድሉ ተጠቃሚዎች መካከል መምህራን፣ የመከላከያ ሠራዊት አባላት፣ የጤና ባለሙያዎች፣ የጸጥታና የህግ ባለሙያዎች ይገኙበታል ተብሏል።

የመኖሪያ ቤት መስሪያ ቦታ ከተሰጣቸው መካከል ቆንጅት ዱጉማ በሰጡት አስተያየት፤ በተለያዩ ጊዜያት የተሰጣቸውን ግዳጅ እንደተወጡና ለሀገር ላበረከቱት ውለታም የቤት መስሪያ ቦታ በማግኘታቸው መደሰታቸውን ገልጸዋል።


የቦታ አሰጣጡ ተግባር ፍትሃዊና ግልጽ መሆኑን የተናገሩት ደግሞ አቶ ጌቱ አዱኛ የተባሉ የጤና ባለሙያ ናቸው።

በማህበር ተደራጅተው ለዓመታት ገንዘብ እንደቆጠቡና ከመንግስት ምላሽ ሲጠባበቁ እንደነበር አስታውሰው፣ ከተማ አስተዳደሩ ለጥያቄያቸው ምላሽ በመስጠቱ ደስተኛ መሆናቸውን ተናግረዋል።


አስተዳደሩ ባስቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ከማህበራቸው አባላት ጋር በመተባበር የቤት ግንባታውን ለመጀመር እየተዘጋጁ መሆኑንም ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.