🔇Unmute
ድሬዳዋ ፤መጋቢት 16/2018 (ኢዜአ)፡- በድሬዳዋ አስተዳደር ገጠር ቀበሌዎች ነዋሪዎችን ከተረጂነት ወደ አምራችነት ለማሸጋገር የተጀመሩ ውጤታማ ተግባራትን አጠናክሮ ለማስቀጠል አመራሩ በቁርጠኝነት መትጋት እንዳለበት ተገለጸ።
በአስተዳደሩ በየደረጃው የሚገኙ የገጠር ክላስተር አመራሮችና ባለሙያዎች የተጀመሩ የበልግና የመኸር ግብርና ስራዎችን አጠናክረው በሚያስቀጥሉበት ጉዳይ ላይ ዛሬ ተወያይተዋል።

በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአስተዳደሩ ምክር ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ አቶ ኢብራሂም ዩሱፍ በዚሁ ወቅት፤ ባለፉት የለውጥ ዓመታት አነስተኛ የመስኖ አውታሮችን ተደራሽ በማድረግ ምርትና ምርታማነትን ለማሳደግ በተሠሩ ሥራዎች አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን ገልጸዋል።
በተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ፣ በሌማት ትሩፋትና በአረንጓዴ አሻራ መርሃ-ግብሮች አማካኝነት በርካቶች ከተረጂነት ወደ አምራችነት እየተሸጋገሩ መሆኑን ጠቁመዋል።
በቀጣይም በአስተዳደሩ ገጠር ቀበሌዎች ከተረጂነት ወደ አምራችነት ለመሸጋገር የተጀመሩ ተግባራት ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስረድተዋል።

የአስተዳደሩ የግብርና፣ ውሃ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ኃላፊ አቶ ኑረዲን አብደላ በበኩላቸው፤ የመጠጥና የመስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ፣ የመስኖ ውሃ መሳቢያ ሞተሮች አቅርቦትና ሙያዊ ድጋፎች ለለውጡ ትልቅ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን ተናግረዋል።
በዘንድሮው ዓመት በሞዴልነት በአራቱ ክላስተሮች የሚተገበረው የገጠር ኮሪደር ልማት ዝግጅት መጠናቀቁን ገልጸው፣ ይህም ለፍራፍሬና ለጥላ ችግኞች ልማት ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር አመልክተዋል።
በመድረኩ ላይ አሁን እየጣለ የሚገኘውን የበልግ ዝናብ በአግባቡ በመጠቀም ለመኸር እርሻ አስፈላጊው ዝግጅት በወቅቱ መጠናቀቅ እንዳለበት አቅጣጫ ተቀምጧል።
በውይይቱ የተሳተፉ የገጠር ክላስተርና ቀበሌ አመራሮች በበኩላቸው፤ የተጀመሩ የልማት ኢኒሼቲቮችና የታቀደውን የኮሪደር ልማት ስኬታማ ለማድረግ በቅንጅትና በቁርጠኝነት እንደሚሠሩ አረጋግጠዋል።
አዲስ አበባ ፤የካቲት 15/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮ-ጅቡቲ የባቡር ትራንስፖርት ተገልጋዮች ፋይዳ መታወቂያን ተጠቅመው በዲጂታል አማራጭ ትኬት የሚቆርጡበት አሰራር ...
Feb 24, 2025
አዲስ አበባ፤ ጥር 03/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ ማሪታይም ባለስልጣን የለማ የትራንስፖርት ኦፕሬተሮችንና የጭነት ባለቤቶችን የሚገናኝ መተግበሪያ አስጀምሯል። ...
Feb 12, 2025