🔇Unmute
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 21/2018(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የአቪዬሽን መሰረተ ልማት በማሟላት የአፍሪካ አቪዬሽን መግቢያ በር መሆን የሚያስችላት ቁመና ላይ ናት ሲሉ የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በረኦ ሀሰን ገለጹ።
ዓለም አቀፉ የአየር ትራንስፖርት ማህበር ከኢትዮጵያ አየር መንገድ እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ጉባኤ በአዲስ አበባ እየተካሄደ ይገኛል።
ለሁለት ቀናት በሚቆየው በዚህ ጉባኤ በአፍሪካ አቪዬሽን ዘርፍ ባሉ ችግሮች እና መፍትሔዎች ላይ ምክክር ይደረጋል።
የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ በረኦ ሀሰን እንደገለጹት፤ አፍሪካ አንድ ነጥብ አራት ቢሊየን የህዝብ ቁጥር ያላት ቢሆንም አህጉሪቱ በበቂ መጠን በአየር ትራንስፖርት ተሳስራለች ማለት አይቻልም።

ለዚህም የዋጋ መጨመር፣ የመሰረተ ልማት በበቂ ደረጃ አለመሟላት እና ወጥ የሆነ የአሰራር ስርዓት አለመኖር ዋነኞቹ ምክንያቶች መሆናቸውን ጠቁመዋል።
ኢትዮጵያ እንደ ሀገር በአቪዬሽን መሰረተ ልማት ላይ በሰፊው ኢንቨስት በማድረግ ላይ መሆኗን በመጠቆም፤ በቢሾፍቱ ግንባታው የተጀመረው ዓለምአቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ፕሮጀክትም ተጠቃሽ መሆኑን ገልጸዋል።
ግንባታው ሲጠናቀቅም የኢትዮጵያን አቅም ከማሳደጉ ባሻገር አፍሪካን ከተቀረው ዓለም ጋር ለማስተሳሰር ጉልህ ሚና እንደሚጫወት አመልክተዋል።
ኢትዮጵያ በአቪዬሽን ዘርፍ መሰረተ ልማት ላይ የምታከናውነው ሥራ ሀገሪቷን የአፍሪካ አቪዬሽን መግቢያ በር (ጌት ዌይ) የሚያደርጋት መሆኑንም ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ ሲቪል አቪዬሽን ባለስልጣን በጠንካራ ሪፎርም ውስጥ እንዲያልፍ መደረጉን ጠቁመው፤ ይህም በኢትዮጵያ ምቹና ደህንነቱ የተጠበቀ የበረራ አገልግሎት እንዲኖር በማድረግ ጠንካራ ተቆጣጣሪ ተቋም እንዲፈጠር ማስቻሉን አብራርተዋል።
በአፍሪካ አቪዬሽን ዘርፍ ለሚስተዋሉ ችግሮች ዘላቂ እልባት ለማበጀት በጋራ መስራት ወሳኝ መሆኑን የገለጹት ሚኒስትር ዴኤታው፤ ችግሮችን ከመለየት ባለፈ ተግባራዊ የመፍትሔ እርምጃዎችን መውሰድ እንደሚገባ አሳስበዋል።
ኢትዮጵያም በመስኩ ያሉ ማነቆዎች እንዲፈቱ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በጋራ ለመስራት ቁርጠኛ መሆኗንም አረጋግጠዋል።

የዓለም አቀፍ ሲቪል አቪየሽን ድርጅት የምሥራቅና ደቡብ አፍሪካ ቀጣና ዳይሬክተር ሉሲ ቡግዋ በበኩላቸው፤ የአፍሪካን የአቪየሽን ትስስር ለማፋጠን ሀገራት በትብብር ሊሰሩ ይገባል ብለዋል።
በአፍሪካ ደኅንነቱ የተጠበቀ የአቪየሽን መሠረተ ልማት ለመገንባት በሚደረገው ጥረት ድጋፍ እንደሚያደርግ ገልጸዋል።

የአፍሪካ አየር መንገዶች ማኅበር ዋና ጸኃፊ አብድራህማን በርቴ፤ የአህጉሪቱን የበራራ ግንኙነት ለማፋጠን በርካታ ሀገራት የአፍሪካ የተቀናጀ የአየር ትራንስፖርት ገበያ የትብብር ማዕቀፍ መፈረማቸውን ገልጸዋል።
ሀገራቱም የትብብር ስምምነት ማዕቀፉን ከመፈረም ባሻገር ወደ ተግባር እንዲለወጥ ኃላፊነታቸውን ሊወጡ ይገባል ብለዋል።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈፃሚ መስፍን ጣሰው በበኩላቸው፤ አየር መንገዱ አህጉሪቱን በአቪየሽን ልማት በማስተሳሰር የሚጠበቅበትን ገንቢ ሚና እየተወጣ ነው ብለዋል።
በቀጣይም ከአፍሪካ የአቪየሽን ኢንዱስትሪ ተዋናዮች ጋር በመተባበር አህጉሪቱን ለማስተሳሰር በቁርጠኝነት እንደሚሰራ አረጋግጠዋል።
ጋምቤላ፤ ነሐሴ 28/2018 (ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል ተግባራዊ የተደረገው የሩዝ ልማት ኢኒሼቲቭ ውጤታማ እየሆነ መምጣቱን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት...
Sep 4, 2026
አሶሳ፤ ነሐሴ 27/2018 (ኢዜአ)፡- በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ኢንዱስትሪዎችን በማስፋፋት ተኪ ምርቶችን የማምረት ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል የክልሉ ርዕሰ ...
Sep 3, 2026
ሆሳዕና፤ ነሀሴ 5/2018 (ኢዜአ)፡-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በተጠናቀቀው በጀት ዓመት ዜጎችን በሥራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ በተከናወኑ ሥራዎች ውጤት መመዝገ...
Aug 12, 2026
አዲስ አበባ፤ነሐሴ 5/2018 (ኢዜአ)፦የመንግሥት በሙስናና ሕገ ወጥ ድርጊት የተሰማሩ አካላትን በሕግ ተጠያቂ የማድረግ ርምጃ ቀጣይነት ሊኖረው እንደሚገባ ኢዜአ...
Aug 12, 2026