🔇Unmute
ጎንደር፤ የካቲት 28/2018 (ኢዜአ)፦በአማራ ክልል አሥር የመንግሥት የመምህራን ትምህርት ኮሌጆችን ወደ ዲጂታል የመማር ማስተማር ሂደት ለማሸጋገር የሪፎርም ሥራዎች እየተከናወኑ መሆናቸውን የክልሉ ትምህርት ቢሮ አስታወቀ፡፡
በክልሉ ኮሌጆች ከስልጠና በተጨማሪ ለቴክኖሎጂና ለሥራ ዕድል ፈጠራ ትኩረት ሊሰጡ ይገባል
ቢሮው በክልሉ የሚገኙ የመምህራን ትምህርት ኮሌጆች በትምህርት ጥራትና በተማሪዎች ማብቃት ዙሪያ ያከናወኗቸውን ተግባራት የሚገመግም መድረክ በጎንደር ከተማ እያካሄደ ነው፡፡
በመድረኩ የቢሮው ምክትል ኃላፊ አቶ ደምስ እድሪስ እንደተናገሩት፤ በክልሉ የሚገኙ የመምህራን ትምህርት ኮሌጆች በእውቀትና በክህሎት የበቁ እጩ መምህራንን ማፍራት እንዲችሉ የሪፎርም ሥራዎች እየተከናወኑ ነው፡፡

የትምህርት ኮሌጆቹ ዘመኑን የዋጀ የመማር ማስተማር ሂደትን ማከናወን እንዲችሉ፣ በተካሄዱ የሪፎርም ሥራዎች የተማሪዎችን ውጤትና የምዝገባ ሥርዓት ሙሉ በሙሉ ወረቀት አልባና የዲጂታል ቴክኖሎጂ ተጠቃሚ ማድረግ ተችሏል ብለዋል፡፡
በተጨማሪም ስድስት የመምህራን ትምህርት ኮሌጆች የቤተ-መጻሕፍት አገልግሎታቸውን ወደ ዲጂታል የአሠራር ሥርዓት መቀየር መቻላቸውን ጠቁመው፤ በቀጣይም ሁሉንም አገልግሎታቸውን ዲጂታል የማድረግ ሥራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተናግረዋል፡፡
የትምህርት ሥርዓቱን ውጤታማ ማድረግ፣ ጥራት ያላቸውና የበቁ መምህራንን ማፍራት እንዲሁም ሥርዓተ-ትምህርቱን በጥናትና ምርምር ማገዝ የሪፎርሙ ዋና የተልዕኮ አካል ተደርጎ እየተሠራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ኮሌጆቹ በአንደኛና በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች ተመድበው ማስተማር የሚችሉና በላቀ እውቀትና ክህሎት የሰለጠኑ መምህራን ማፍራት እንዲችሉም ሰፊ ድጋፍ እየተደረገላቸው ነው ብለዋል፡፡
ኮሌጆቹ የክልሉን የመምህራን ፍላጎት መሠረት በማድረግ በአሁኑ ወቅት በዲፕሎማና በዲግሪ መርሃ ግብር ከ10 ሺህ በላይ እጩዎችን በመምህርነት ሙያ እያሰለጠኑ እንደሚገኝም አስረድተዋል፡፡

የጎንደር መምህራን ትምህርት ኮሌጅ ዲን አቶ የሻምበል ፀሐይ በበኩላቸው እንደገለጹት፤ ከተመሠረተ 44 ዓመታት ያስቆጠረው ኮሌጁ ከ64 ሺህ በላይ መምህራንን አሰልጥኖ በማስመረቅ ለትምህርት ጥራት መረጋገጥ የድርሻውን አበርክቷል፡፡
ኮሌጁ በዘንድሮ ዓመት በመደበኛውና በማታው የትምህርት ክፍለ ጊዜ በዲፕሎማና በዲግሪ መርሃ ግብር ከ3 ሺህ 400 በላይ መምህራን እያሰለጠነ መሆኑን ጠቁመው፣ የተማሪዎችን የምዝገባ ሥርዓት ወደ ዲጂታል ማሸጋገር መቻሉን ገልጸዋል፡፡
በእውቀት፣ በክህሎትና በአመለካከት የበቃ ውጤታማ ትውልድ ለማፍራት የመምህራን የሥልጠና ሥርዓት ዘመኑን በዋጀ የዲጂታል ቴክኖሎጂ መመራት አለበት ያሉት ደግሞ የደብረ ብርሃን መምህራን ትምህርት ኮሌጅ ዲን መባ ፈጠነ (ዶ/ር) ናቸው፡፡

ኮሌጁ ከተመሠረተ አንሥቶ ከ60 ሺህ በላይ የአንደኛ ደረጃ መምህራንን አሰልጥኖ ማሰማራቱን ጠቁመው፣ አሁን ላይ የመማር ማስተማር ሥራውን ዲጂታላይዝ ማድረግ የሚያስችሉ የሪፎርም ሥራዎችን እያከናወነ ይገኛል ብለዋል፡፡
ለሁለት ቀናት በሚቆየው የግምገማ መድረክ ላይ ከክልሉ 10 ኮሌጆች የተውጣጡ ዲኖችና የትምህርት አመራሮችን ጨምሮ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ተሳታፊ ሆነዋል፡፡
አዲስ አበባ፤ የካቲት 20/2017(ኢዜአ)፦ ተቋማት ከሚሰጡት አገልግሎት በተጨማሪ ተቋማቸውን ለተገልጋዮች ምቹ ሊያደርጉ እንደሚገባ የሐረሪ ክልል ርዕሰ መስተዳድ...
Feb 28, 2025
ወልቂጤ፤ የካቲት 20/2017 (ኢዜአ):-በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የህብረተሰቡን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የመንገድ መሰረተ ልማት ስራዎች ...
Feb 28, 2025
አዲስ አበባ፤ የካቲት 20/2017 (ኢዜአ)፦ የስፔስ ሳይንስና ጂኦስፓሻል ኢንስቲትዩት ከኢትዮጵያ ኮሙኒኬሽን ባለስልጣን ጋር በመሬት ምልከታ እና በኮሙኒኬሽን ሳ...
Feb 28, 2025
ጋምቤላ ፤የካቲት 17/2017 (ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል ባለፉት ዓመታት ተጀምረው ያልተጠናቀቁ ነባር ፕሮጀክቶችን አጠናቆ ወደ ስራ ለማስገባት የሚያስችሉ እርም...
Feb 24, 2025