የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

የውጭ ሀገር የሥራ ስምሪት ሥርዓትንና ሕግን አክብሮ ከተተገበረ የዜጎችን፣ የሀገርንና የተቋማትን ተወዳዳሪነት ማሳደግ ይቻላል - ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል

Apr 14, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 4/2017(ኢዜአ)፦ የውጭ ሀገር የሥራ ስምሪት ሥርዓትንና ሕግን አክብሮ መተግበር ከተቻለ የዜጎችን፣ የሀገርንና የተቋማትን ተወዳዳሪነት ማሳደግ ይቻላል ሲሉ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል ገለጹ፡፡

የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር በቀረፀው የውጭ ሀገር ሥራ ስምሪት ረቂቅ አዋጅ ዙሪያ ከውጭ ሀገር የሥራና ሠራተኛ አገናኝ ኤጀንሲዎች ጋር ውይይት አካሂዷል፡፡

በመድረኩ የተገኙት የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሃት ካሚል የውጭ ሀገር የሥራ ስምሪት ሥርዓትንና ሕግን አክብሮ መተግበር ከተቻለ የዜጎችን፣ የሀገርንና የተቋማትን ተወዳዳሪነት ማሳደግ ይቻላል ብለዋል፡፡


ሚኒስቴሩ ሥነ-ምህዳሩን ምቹ በማድረግ ኤጀንሲዎች ሚናቸውን እንዲወጡ ለማድረግ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን እያከናወነ እንደሚገኝ መግለጻቸውን የሚኒስቴሩ መረጃ ያመላክታል፡፡

በተጨማሪም ኢንዱስትሪውን ለመቀየር ብቁ የኤጀንሲዎች ስብስብ በማፍራት የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በላቀ ትጋት እየሠራ እንደሚገኝም አብራርተዋል፡፡

ይሁን እንጂ በዘርፉ የተፈጠረውን ምቹ ሁኔታ በመጠቀም ሚናቸውን በኃላፊነት ከመወጣት ይልቅ ሕጋዊ አሰራርን በማይከተሉ ኤጀንሲዎች ሳቢያ ዜጎችን ለእንግልትና ለስቃይ የሚዳርጉ አጋጣሚዎች በተደጋጋሚ መከሰታቸውን ጠቁመዋል፡፡

መሰል ሕገ-ወጥ ድርጊቶችን በመከላከል የዜጎችን ክብርና ደህንነት ማዕከል ያደረገ የውጭ ሀገር ሥራ ስምሪት ሥርዓት እውን ለማድረግ የአዋጅ ማሻሻያ ማድረግ አስፈላጊ ሆኖ መገኘቱንም ጠቁመዋል፡፡


ሕጋዊ አሠራርን ተከትለው ለዜጎች ተገቢውን አገልግሎት ለሚሰጡ ኤጀንሲዎች እውቅና መስጠት የሚያስችል አሠራር ለመዘርጋት ጥናት እየተካሄደ መሆኑን ሚኒስትሯ ገልጸዋል፡፡

አሁን በሥራ ላይ የሚገኙ ኤጀንሲዎችን በማሰባሰብ የተሻለ አቅም እንዲፈጥሩ የሚያግዝ ወጥ የሆነ አደረጃጀት በቀጣይ ለመፍጠር መታቀዱን መናገራቸውም በመረጃው ተመላክቷል፡፡

የውጭ ሀገር የሥራ ሥምሪት በፍጹም ሥነ ምግባር፣ በሃላፊነትና ሀገርን በመውደድ ስሜት ሊተገበር እንደሚገባም ነው ሚኒስትሯ ያሳሰቡት፡፡

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.