🔇Unmute
አዳማ፤ ጥቅምት 19/2018(ኢዜአ)፡- የኮሪደር ልማቱ የከተማዋን ነዋሪዎች የልማት ተጠቃሚነት ይበልጥ ለማሳደግ ምቹ መደላድል የፈጠረ መሆኑን የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሃይሉ ጀልዴ አስታወቁ።
በከተማዋ የመጀመሪያው ዙር የኮሪደር ልማት ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል ።
የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሃይሉ ጀልዴ በወቅቱ ባደረጉት ንግግር፤ የተሟላ መሰረት ልማት ያላት ውብ፣ ንፁሕና ያማረች አዳማን ለመገንባት የተጀመረው ስራ በሕዝቡ ተሳትፎ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።

ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት የተደረገው የመጀመሪያው ዙር የኮሪደር ልማቱ የከተማዋን ነዋሪዎች የልማት ተጠቃሚነት በተሻለ ደረጃ ይበልጥ ለማሳደግ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን አስታውቀዋል።
ይህም ልማት 19 ነጥብ 2 ኪሎ ሜትር ርዝመት እና 23 ሜትር ስፋት ያለው የአስፋልት ኮንክሪት፣ የእግረኛና የብስክሌት መንገድ ግንባታ መሆኑን ገልጸዋል።
መንገዱ ከዛሬ ጀምሮ ለተሽከርካሪዎች፣ ለብስክሌትና ለእግረኞች ክፍት መሆኑንም ከንቲባ ሃይሉ ጀልዴ ይፋ አድርገዋል።
ክፍት ከተደረጉት መሰመሮች ውስጥ ከኦሮሚያ ፖሊሲ ኮሌጅ እስከ ደራርቱ አደባባይ ያለው ይገኝበታል።
የመጀመሪያው ዙር የኮሪደር ልማቱ ሥራ በከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር የተቀመጠውን ደረጃ አሟልቶ በጥራት መከናወኑን ጠቅሰው፤ በተጨማሪም ስማርት የመብራት ምሰሶዎች፣ አረንጓዴ ፓርኮችና ተያያዥ የመንገድ ዳር የማስዋብ ተግባራት መከናወናቸው አንስተዋል።
በመሰረተ ልማት፣ በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማት የተለወጠችና ያደገች ከተማን ለትውልድ ለማስተላለፍ ግብ አድርገን እየሰራን ነው ብለዋል።
የኮሪደር ልማቱ ተጠናክሮ ይቀጥላል ያሉት ከንቲባው፤ ባለሃብቶችና ነዋሪዎችን ጨምሮ ሌሎችም ባለድርሻ አካላት በልማቱ ላይ ሲያደርጉ የቆዩትን ተሳትፎ አጠናክረው እንዲቀጥሉም መልዕክት አስተላልፈዋል።
ከከተማው ነዋሪዎች መካከል አቶ አማን ሲራጅ በሰጡት አስተያየት፤ ከተማዋ አሁን የሚመጥናትን ልማት እያገኘች ጥሩ ገፅታ እየተላበሰች ትገኛለች ብለዋል።
በከተማዋ ከዋናው መስመር ጀምሮ የበስክሌትና እግረኛ መንገድ እንዳልነበረ አስታውሰው፤ አሁን የኮሪደር ልማት በመሰራቱ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን ተናግረዋል።
አቶ ወሰኔ ቶሎሳ በበኩላቸው፤ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በከተማዋ የተከናወኑና በመከናወን ላይ የሚገኙ የልማት ተግባራት አበረታች መሆናቸወን ተናግረዋል።
ከመንግሥት ጎን በመሆን የተጀመሩ የልማት ተግባራት ይበልጥ በተሻለ ደረጃ እንዲያድጉ ድጋፋቸውን በትብብርና በቅንጅት እንደሚያጠናክሩም አስተያየት ሰጪዎቹ ገልጸዋል።
የመጀመሪያው ዙር የኮሪደር ልማት ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት በተደረገበት ሥነ-ሥርዓት ላይ የከተማ አስተዳደሩ አመራሮችና ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
አዲስ አበባ፤ የካቲት 21/2017(ኢዜአ)፡- የምግብ ዋስትና እና ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ ለነገ የሚተው የምርጫ ጉዳይ ባለመሆኑ በልዩ ትኩረት መረባረብ እንደሚገባ...
Feb 28, 2025
ሐረር፤ የካቲት 16/2017(ኢዜአ)፦ ባለፉት ዓመታት የተከናወኑ ሁሉን አቀፍ ስራዎች የህዝቡን ተጠቃሚነት ያሳደጉ መሆናቸውን የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አ...
Feb 24, 2025
አዲስ አበባ፤ ጥር 30/2017(ኢዜአ)፦የየካቲት ወር የነዳጅ ምርቶች የችርቻሮ መሸጫ ዋጋ በጥር ወር በነበረበት የሚቀጥል መሆኑን የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስ...
Feb 8, 2025