የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
የአፍሪካ ህብረት

በድሬዳዋ አደጋዎችን በራስ አቅም ለመሻገር የሚያስችሉ ተግባራት በቅንጅት እየተሰሩ ነው

Dec 8, 2025

IDOPRESS

🔇Unmute

ድሬደዋ፤ ሕዳር 28/2018 (ኢዜአ)፡-በድሬዳዋ አስተዳደር በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ከማረጋገጥ ባሻገር የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ አደጋዎችን በራስ አቅም ለመሻገር የሚያስችሉ ተግባራት በቅንጅት እየተከናወኑ መሆኑን የአስተዳደሩ ግብርና፣ ውሃ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ አስታወቀ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሰሞኑን በከፍተኛና መካከለኛ አመራሮች ስልጠና ላይ፤ ሀገራችን ያሏትን ፀጋዎችና ሀብቶች በዕውቀትና በጥበብ ጥቅም ላይ በማዋል የምግብ ሉአላዊነት የማረጋገጥ ጉዞ ተጠናክሮ መቀጠሉን አንስተዋል።

ጦም ያደረን መሬት ወደ ልማት በማስገባትና ፀጋዎችን በሙሉ ወደ ምርታማነት በመቀየር የምግብ ሉአላዊነት ማረጋገጥና ለገበያ ተደራሽ በማድረግ፣ የሚከሰቱ ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋዎችን በራስ አቅም ምላሽ የመስጠት ጉዳይ ወሳኝ መሆኑን አስምረውበታል።

የድሬዳዋ አስተዳደር ግብርና፣ ውሃ፣ ማዕድንና ኢነርጂ ቢሮ ኃላፊ አቶ ኑረዲን አብደላ ለኢዜአ እንዳሉት፤ በአስተዳደሩ የተፈጥሮ ፀጋዎችን በተቀናጀ መንገድ በመጠቀም በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ዋስትናን የማረጋገጥ ጉዞ ስኬታማ እየሆነ ይገኛል።


በተለይም በአረንጓዴ አሻራ፣ በአፈርና ውሃ ጥበቃ፣ በሌማት ትሩፋት፣ በመስኖና በእንሰሳት ልማት እየተከናወኑ የሚገኙ ተግባራት ከተረጂነት በመላቀቅ የምግብ ሉአላዊነት ማረጋገጥ እያስቻሉ ናቸው።

በዚህም በአስተዳደሩ የገጠር ክላስተር ያሉ ማህበረሰቦች በልመና የመኖርን ተግባር በመጠየፍና ከሴፍትኔት ተረጂነት እየወጡ በቤተሰብ ደረጃ የምግብ ሉአላዊነት እያረጋገጡ መሆኑን አንስተዋል።

ለሚያጋጥሙ የተፈጥሮ እና የሰው ሰራሽ አደጋዎች የቅድመ ማስጠንቀቂያ ጠንካራ ስርአት በመዘርጋት ከአደጋ የተጠበቀ አይበገሬ ማህበረሰብ በተቀናጀ መንገድ የመገንባት ስራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል።

ለሚከሰቱ ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋዎች በራስ አቅም ምላሽ ለመስጠት እየተከማቸ ከሚገኘው እህል ባሻገር ለመጠባበቂያነት የሚውል ምርት በአስተዳደሩ 10 ሄክታር መሬት ላይ እየለማ መሆኑን ተናግረዋል።

ካለፈው አንድ አመት ጀምሮ በአርብቶአደሩ መንደሮች እየተከናወኑ የሚገኙ የግጦሽ፣ የውሃና የፍራፍሬ ልማቶች ማህበረሰቡን ከእንስሳትና ከመሬት ሃብቱ ተጠቃሚ እያደረጉት መሆናቸውን የገለፁት ደግሞ በቢሮው የአርብቶና ከፊል አርብቶአደር ኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት አስተባባሪ አቶ ኢሳን ሁሴን ናቸው።


የድሬደዋ አስተዳደር አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን የአደጋ ስጋት ቅነሳ ዳይሬክተር አቶ አብዱሰላም የሱፍ በበኩላቸው፤ የትኛውንም አደጋ በራስ አቅም ለመሻገር የሚያስችሉ አደረጃጀቶች፣ አሠራሮችና ደንብ ተዘጋጅተው እየተሰሩ የሚገኙ ስራዎች ውጤት እያስገኙ ናቸው።

በአስተዳደሩ ደረጃ ሁሉም ሴክተሮች የሚሳተፉበት የአደጋ ስጋት አመራር ምክር ቤት በማቋቋምና በየደረጃው የሚገኘውን ህብረተሰብ በማሳተፍ፣ ከአመራሮችና ሠራተኞች እንዲሁም ከንግዱ ማህበረሰብ ከገቢያቸው ገንዘብ በማዋጣት የድርሻቸውን እያበረከቱ መሆናቸውን አንስተዋል።

በአሁኑ ጊዜም በተዘጋጁ መጋዘኖች የመጠባበቂያ እህል እና ተገቢው ገንዘብ እየተሰበሰበ መሆኑን ጠቅሰው ዘመን የተሻገረው የእርስ በእርስ መደጋገፍና መረዳዳት ባህልን በማፅናት በራስ አቅም ችግርን የመሻገሩ ጉዞ ይጠናከራል ብለዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.