የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
የአፍሪካ ህብረት

በአዳማ ከተማ በግማሽ ዓመቱ ከ64 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል ተፈጥሯል

Jan 16, 2026

IDOPRESS

🔇Unmute

አዳማ ፤ ጥር 8/2018 (ኢዜአ)፡- በአዳማ ከተማ በግማሽ ዓመቱ ከ64 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል መፈጠሩን የከተማዋ የስራ እድል ፈጠራና ክህሎት ጽሕፈት ቤት ገለፀ።

በማህበር ተደራጅተው ወደ ስራ ለገቡ ዜጎች ከ1 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር በላይ ብድር በመስጠት ከ2 ሺህ በላይ የሚሆኑ ኢንተርፕይዞችን ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉም ተገልጿል።

የአዳማ ከተማ አስተዳደር የስራ እድል ፈጠራና ክህሎት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አብዱልቃድር ጠይብ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በከተማዋ የስራ አጥነት ችግርን ለመቅረፍ በልዩ ትኩረት እየተሰራ ነው።


በዚህም በግማሽ ዓመቱ 64 ሺህ የሚሆኑ ዜጎች የስራ እድል ማግኘታቸውን ጠቅሰው ወደ ስራ ከገቡት ውስጥ 31 ሺህ የሚሆኑት በቋሚ ቅጥር የስራ እድል የተፈጠረላቸው መሆኑን ተናግረዋል።

የተቀሩት ደግሞ በማህበር ተደራጅተው በተለያዩ የስራ መስኮች መሰማራታቸውን የገለፁት ኃላፊው አገልግሎት፣ ብረታ ብረት፣ የእንጨት ስራ፣ ንግድ፣ ግንባታ፣ የወተት ላሞችና ዶሮ እርባታ፣ በከብት ማድለብ፣ በንብ ማነብና በግብርና ዘርፍ መሰማራታቸውን ገልጸዋል።

በተጨማሪም ማኑፋክቸሪንግ፣ ጎጆ ኢንዱስትሪና ጨርቃ ጨርቅ በስፋት የስራ እድል ከተፈጠረባቸው መስኮች መካከል መሆናቸውን ተናግረዋል።

በማህበር ተደራጅተው ወደ ስራ ለገቡ ዜጎች ከ1 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር በላይ ብድር በመስጠት ከ2 ሺህ በላይ የሚሆኑ ኢንተርፕይዞች የብድር አገልግሎቱ ተጠቃሚ መሆናቸውንም አስረድተዋል።


ስራ እድል ለተፈጠረላቸው ዜጎች ለዶሮና የወተት ላሞች እርባታ የሚውሉ ሼዶች መተላለፋቸውን ገልጸው በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ለተሰማሩትም የሊዝ ማሽን መቅረቡን አውስተዋል።

በከተማው የስራ እድል ከተፈጠረላቸው ወጣቶች መካከል ወጣት ቦጋለ ለገሰ እንደገለጸው፤ መስተዳደሩ በፈጠረላቸው ምቹ ሁኔታዎች በመጠቀም በቤተሰብ ደረጃ በማህበር ተደራጅተው ወደ ስራ ገብተዋል።

በራሳችን መሬት ላይ ቤተሰብን በማስተባበር በማህበር ተደራጅተን የዱቄት ፋብሪካ በማቋቋም ወደ ስራ ገብተናል ያለው ወጣት ቦጋለ በብድር እና በራሳቸው በ35 ሚሊዮን ብር የዱቄት ፋብሪካ አቋቁመው ወደ ምርት መግባታቸውን ተናግሯል።

በፋብሪካው ለ25 ዜጎች የስራ እድል መፈጠሩንም ነው የገለጸው።

ከተማ አስተዳደሩ ብድር ከማመቻቸት ባለፈ መብራት፣ ውኃና መንገድን ጨምሮ መሰረተ ልማትን እንዳሟላላቸው ተናግሯል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.