የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ፖለቲካ እና ደህንነት

የጅማ - ጭዳ የመንገድ ፕሮጀክት ግንባታ ምን ደረጃ ላይ ነው?

Jan 13, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ ጥር 4/2017(ኢዜአ)፦ የጅማ - ጭዳ 80 ኪሎ ሜትር የመንገድ ግንባታ ፕሮጀክት ወደ አስፋልት የማንጠፍ ምዕራፍ መሸጋገሩን የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ገልጿል።

የመንገድ ግንባታ ፕሮጀክቱ የኦሮሚያ እና የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ህዝቦች ክልሎች ሶስት ወረዳዎችን የሚያስተሳስር መሆኑም ተመላክቷል።

የመንገድ ፕሮጀክቱ አሁን ላይ የ10 ኪሎ ሜትር የአስፋልት ንጣፍ ስራ መከናወኑንም አስተዳደሩ አስታውቋል።

መንገዱ የጨበራ ጩርጩራ ብሔራዊ ፓርክ እና የሃላል ኬላ መዳረሻ በመሆኑ ለቱሪስቶች ምቹ ከማድረግ አኳያ ጉልህ አስተዋጽዖ የሚያበረክት መሆኑንም ጠቁሟል።


በተጨማሪም የ14 ኪሎ ሜትር ሰብቤዝ፣ 11 ኪሎ ሜትር ቤዝኮርስ እና የ52 በመቶ የአፈር ቆረጣ እና ሙሌት ሥራዎች መሰራታቸውንና የአንድ ድልድይ ግንባታ ሂደት ላይ እንደሚገኝም ገልጿል።

የመንገዱ ግንባታ አጠቃላይ አፈጻጸም 31 በመቶ መድረሱንም አስተዳደሩ አስታውቋል።

የፕሮጀክቱን የተሻለ አፈጻጸም አጠናክሮ ለማስቀጠል በማሽነሪ፣ የሰለጠነ ባለሞያ ቅጥር እና በግብአት በኩል በቂ ዝግጅት መደረጉን ቦታው ድረስ በተደረገ ቅኝት መመልከት መቻሉንም አረጋግጧል።

በተጨማሪም ግንባታው የአካባቢውን ሥነ-ምኅዳር ባገናዘበ መልኩ የአካባቢ እና የማኅበራዊ ደኅንነት መርሆዎችን ተከትሎ በጥንቃቄ እየተከናወነ ይገኛል ብሏል አስተዳደሩ።


ቻይና ቲሲጁ ኢንጂነሪንግ ግንባታውን እያከናወነ መሆኑንና ኪዮንግዶንግ ኢንጂነሪንግ፣ ኦሪየንታል ኮንሰልቲንግ እና ኮር ኮንሰልቲንግ የማማከር እና የቁጥጥር ሥራውን በጥምረት እንደሚሰሩም ጠቁሟል።

ለግንባታው የተመደበው 2 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር በአፍሪካ የልማት ፈንድ እና በጃፓን ዓለም-አቀፍ የልማት ተራድዖ ድርጅት የፋይናንስ ድጋፍ እንደሚሸፈንመ አስተዳደሩ በመረጃው አስታውቋል።

መንገዱ ሲጠናቀቅ ቀድሞ ከጅማ ከተማ እስከ ጭዳ ከተማ ለመድረስ የሚወስደውን 4 ሰዓት የጉዞ ጊዜ ከአንድ ሰዓት ተኩል ባነሰ መግባት እንደሚያስችልና የጅማ፣ ዴዶ፣ ሚቴሶ እና መሰል ከተሞች ትስስርን በማጠናከር ምርት በቀላሉ ወደ ማዕከላዊ ገበያ ለማድረስ እንደሚያስችልም በመረጃው ተመላክቷል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.