የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ፖለቲካ እና ደህንነት

<p>በጋምቤላ ክልል የተጀመሩ የመንገድ ፕሮጀክቶችን አፈፃፀም ለማፋጠን በትኩረት እየተሰራ ነው</p>

Jan 18, 2025

IDOPRESS

ጋምቤላ፤ ጥር 9/2017(ኢዜአ)፦ በጋምቤላ ክልል የተጀመሩ የመንገድ ፕሮጀክቶችን አፈፃፀም በማሻሻል የማህበረሰቡን የመሰረተ ልማት ጥያቄዎች ለመመለስ በትኩረት እየሰራ መሆኑን የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር ገለጸ።

አስተዳደሩ በክልሉ ከ10 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ እየተገነቡ በሚገኙ ዘጠኝ የመንገድ ፕሮጀክቶች ዙሪያ ከክልሉ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ጋር ዛሬ በጋምቤላ ከተማ ተወያይቷል።


የአስተዳደሩ ዋና ዳይሬክተር ኢንጂነር መሀመድ አብዱራህማን በውይይቱ ላይ እንደገለጹት አስተዳደሩ ውስጣዊ አሰራሮችን በማጠናከርና የፕሮጀክት ፈፃሚዎችን በማትጋት የመንገድ ፕሮጀክቶችን አፈፃፀም ለማሻሻል በትኩረት እየሰራ ነው ብለዋል።

በክልሉ በሂደት ላይ የሚገኙትን የመንገድ ፕሮጀክቶች በማፋጠንና ተጀምረው በአፈፃፀም ችግር የተቋረጡትን በማስቀጠል ለህዝቡ የመንገድ መሰረተ ልማት ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት በትጋት እንደሚሰራም አረጋግጠዋል።

አስተዳደሩ በክልሉ እያከናወናቸው ለሚገኙት የመንገድ ፕሮጀክቶች ስኬታማነት የክልሉ መንግስት ድጋፍና ትብብር እንዲጠናከር ዋና ዳይሬክተሩ ጠይቀዋል።


በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ ዓለሚቱ ኡሞድ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት ክልሉ ቀደም ሲል በነበሩት ዓመታት የተፈለገውን ያህል የመንገድ መሰረተ ልማት ተደራሽ ሳይሆን ቆይቷል።

ይሁን እንጂ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የክልሉን ህዝብ የመንገድ መሰረተ ልማት ጥያቄዎች ለመፍታት በፌዴራል መንግስት የተጀመሩት ስራዎች የሚበረታቱ ቢሆንም በተወሰኑ የመንገድ ፕሮጀክቶች ላይ የአፈፃፀም ችግሮች መኖራቸውን ገልጸዋል።

በመሆኑም የኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር በክልሉ በሂደት ላይ የሚገኙ መንገዶች ግንባታን ለማፋጠንና የተቋረጡትን ለማስቀጠል የክልሉ መንግስት ድጋፉን አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።


በኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር የእቅድና ፕሮግራም አስተዳደር ዳይሬክተር ወይዘሮ ቆንጅት ዓለሙ በመድረኩ ላይ ባቀረቡት ሪፖርት በክልሉ ከ10 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ ዘጠኝ የአስፓልት መንገድ ፕሮጀክቶች ግንባታ ተጀምረው እንደነበር ተናግረዋል።

ከ580 ኪሎ ሜትር በላይ ርዝመት ካለቸው ዘጠኝ የመንገድ ፕሮጀክቶች መካከል አምስቱ በግንባታ ሂደት ላይ መሆናቸውን ጠቅሰው ቀሪዎቹ በአፈፃፀም ችግርና በሌሎች ምክንያቶች መቋረጣቸውን ገልጸዋል።


በግንባታ ሂደት ላይ ከሚገኙት ፕሮጀክቶች መካከል ከጋምቤላ አቦቦ ፑኝውዶ፣ ከፑኝውዶ ጊሎ ራድ፣ ከላሬ ጂካዎ፤ ከፑኝውዶ ጆር አንጌላ ሲሆኑ ከተቋረጡት ፕሮጀክቶች መካከል ደግሞ ከኮኮሪ -መንገሺ- ሜጢ- ኩቢጦ፣ከጋምቤላ ኢሊያ፣ ከኢሊያ መኮይና ሌሎች እንደሚገኙበት ተናግረዋል።

በዘንድሮው ዓመት በሂደት ላይ ከሚገኙት ፕሮጀክቶች መካከል ሁለቱን ለማጠናቀቅና በሂደት ላይ ያሉትን ደግሞ ለማፋጠን እንዲሁም በተለያዩ ምክንያቶች የተቋረጡትን ለማስቀጠል እየተሰራ መሆኑንም አመላክተዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.