የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

<p>በደቡብ ወሎ ዞን በዘንድሮው  የበልግ ወቅት ከ104 ሺህ በላይ ሄክታር መሬት ይለማል</p>

Feb 6, 2025

IDOPRESS

ደሴ ኢዜአ ጥር 28/2017-- በደቡብ ወሎ ዞን በዘንድሮው የበልግ ወቅት ከ104 ሺህ 600 በላይ ሄክታር መሬት እየታረሰ መሆኑን የዞኑ ግብርና መምሪያ አስታወቀ።

የመምሪያው የሰብል ልማት ቡድን መሪ አቶ ይመር ሰይድ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ አርሶ አደሩ የሰብል ምርታማነትን በማሳደግ የምግብ ዋስትናውን እንዲያረጋግጥ በትኩረት እየተሰራ ነው።

በዘንድሮው የበልግ ወቅት ከ104 ሺህ 600 ሄክታር የሚበልጥ መሬት እየታረሰ ሲሆን፤በሚቀጥለው ወር የዘር ስራ እንደሚጀመር ተናግረዋል፡፡


በበልግ ወቅቱ ከሚለማው መሬት ከሁለት ሚሊዮን ኩንታል በላይ ምርት ለማምረት መታቀዱንም ነው የተናገሩት።

ምርታማነትን ለማሳደግም ከሁለት ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ በላይ የተፈጥሮ ማዳበሪያን ጨምሮ የፋብሪካ ማዳበሪያም ለአርሶ አደሩ ተደራሽ ተደርጓል ብለዋል።

በዞኑ ለጋምቦ ወረዳ የቀበሌ 14 ነዋሪ አርሶ አደር በላይ አህመድ፤ በአንድ ሄክታር ተኩል መሬት ላይ ገብስ፣ ስንዴና ጤፍ ለማልማት የእርሻ ሥራ አጠናቀዋል፡፡

ከሚያለሙት መሬትም ከ30 ኩንታል በላይ ምርት እንደሚጠብቁ ጠቁመው፤ ባለፈው ዓመት ከዚህ መሬት 26 ኩንታል ምርት ማግኘታቸውን አስታውሰዋል።

የበልግ ዝናብ ምርታማነትን በማሳደግ ተጠቃሚ እያደረጋቸው መሆኑን የተናገሩት ሌላው የደሴ ዙሪያ ወረዳ አርሶ አደር ከድር ሙሄው ናቸው።

በዘንድሮ የበልግ ወቅትም አንድ ሄክታር መሬት በገብስ፣ ስንዴና ባቄላ ዘር ለመሸፈን የእርሻ ስራ በማጠናቀቅ የዝናቡን መጣል እየተጠባበቁ ይገኛል፡፡


ከልማቱ ከ20 ኩንታል በላይ ምርት ለማግኘት የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ማዳበሪያ ማዘጋጀታቸውን ገልጸዋል፡፡

በዞኑ ባለፈው ዓመት በበልግ ወቅት ከለማው 105 ሺህ ሄክታር መሬት 1 ነጥብ 8 ሚሊዮን ኩንታል ምርት መገኘቱን ከመምሪያው የተገኘ መረጃ ያመለክታል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.