የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

<p>የኢንቨስትመንትን ማበረታቻ ስርአቶች ለታለመላቸው አላማ እየዋሉ መሆናቸውን ማረጋገጥ ይገባል</p>

Feb 6, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ጥር 28/2017(ኢዜአ)፦የኢንቨስትመንትን ማበረታቻ ስርአቶች ለታለመላቸው አላማ እየዋሉ መሆናቸውን ማረጋገጥ እንደሚገባ የመንግስት ወጪ አስተዳደር እና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ።


በቋሚ ኮሚቴው የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን የ 2015/16 በጀት አመት የኢንቨስትመንት ፈቃድ አሰጣጥ፣ድህረ ኢንቨስትመንት ክትትል እና የኢንቨስትመንት ማበረታቻ መብት አጠቃቀምን በተመለከተ የክዋኔ ኦዲት ሪፖርት ላይ ተወያይቷል።


የቋሚ ኮሚቴው አባላት በሪፖርቱ በቀረቡ ጉዳዮች ላይ ጥያቄ አቅርበው በኮሚሽኑ የበላይ አመራሮች ምላሽ እና ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል።


በውጭ ዜጎች የተያዙ የስራ መደቦችን ለተተኪ ኢትዮጵያውያን የማሸጋሸግ ስራ አለመከናወኑና ለዚህም የሚያግዝ የስልጠና መርሃ ግብር አለመዘጋጀቱን መመልከታቸውን ተናግረዋል።


የኢንቨስትመንት ፈቃድ የማደስ እና የመሰረዝ ስራዎች በተቀመጡ ህጎች መሰረት በፍጥነት በማከናወን ወደ ምርት እንዲሸጋገሩ የሚደረገው ድጋፍ እና ክትትል አጥጋቢ አለመሆኑን አንስተዋል።


ከቀረጥ ነጻ ወደ ሀገር የገቡ የካፒታል፣ የግንባታ እቃዎችና መለዋወጫዎች ለታለመላቸው አላማ መዋላቸውን በመከታተል ረገድ ክፍተት መኖሩን ጠቁመዋል።


በተገቢው መንገድ የኢንቨስትመንት እድሎችን አለማስተዋወቅ እና ለዚህም የሚሆን የዲጂታል አሰራር አለመዘርጋቱ በኦዲት ሪፖርቱ መመላከቱን አንስተዋል።


የሁለትዮሽ የኢንቨስትመንት ማስፋፊያ እና ጥበቃ ስምምነቶች በተያዘላቸው ጊዜ አለመፈረማቸው በግኝቱ መመላከቱን ጠቁመዋል።


የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘለቀ ተመስገን (ዶ/ር) በሰጡት ምላሽና ማብራሪያ፥ የኦዲት ሪፖርቱን መነሻ በማድረግ በርካታ የማስተካከያ እርምጃዎች መወሰዳቸውን ገልጸዋል።


በዚህም በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ የሚያጋጥሙ ችግሮችን ለመፍታት ቅንጅታዊ አሰራር እየተተገበረ መሆኑን ጠቁመዋል።


ከውጭ አገራት ዜጎች የስራ ስምሪት ጋር በተያያዘ አስገዳጅ ሁኔታ ሲኖር ብቻ እድሳት የሚደረግበት አሰራር መኖሩን ተናግረዋል።


የመረጃ ፍሰቱን የተሳለጠ ለማድረግ በቀጣዮቹ ሁለት ወራት የሚጠናቀቅ ዲጂታል ስርአት እንደሚዘረጋ አመላክተዋል።


የሁለትዮሽ የኢንቨስትመንት ማስፋፊያ እና ጥበቃ ስምምነቶችን መልሶ የመገምገም ስራ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመው፥ የተጠናቀቁት ተፈርመው መጽቃቸውን አንስተዋል።


የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሰረት ዳምጤ ኮሚሽኑ ከክልል እና ከተማ አስተዳደሮች ጋር የአሰራር ስርአት መዘርጋት እንዳለበት ተናግረዋል።


ከውጭ ኢንቨስትመንት የእውቀት፣የክህሎት እና የቴክኖሎጂ ሽግግር የሚጠበቅ መሆኑን በመጥቀስ በዚህ ረገድ የእውቀት ሽግግር ማድረጋቸውንና ያላቸውን አቅም ማረጋገጥ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።


የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ወጪ አስተዳደር እና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የሺመቤት ደምሴ (ዶ/ር) የሚደረጉ ስምምነቶች የኢትዮጵያን ጥቅም ያስጠበቁ መሆናቸውን ማረጋገጥ እንደሚገባ አስገንዝበዋል።


ኢንቨስትመንትን ለማበረታት የሚደረጉ ስርአቶች ለታለመላቸው አላማ እየዋሉ መሆናቸውን ማረጋገጥ እንደሚገባ ነው የተናገሩት።


ተቋሙ ማስተካከያ የተደረገባቸውን እና ሳይስተካከሉ የቀሩ የኦዲት ግኝቶችን በድርጊት መርሃ ግብር በመለየት እስከ የካቲት 15 ቀን 2017 ዓ.ም ድረስ ለቋሚ ኮሚቴው እንዲያቀርብ አቅጣጫ ሰጥተዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.