የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ፖለቲካ እና ደህንነት

<p>ኮሌጁ በለውጥ ሥራዎቹ የግብዓት ችግሮቹን በራስ አቅም መፍታት መቻሉን አስታወቀ</p>

Feb 13, 2025

IDOPRESS

ሀዋሳ ፤ የካቲት 5/2017 (ኢዜአ):- በሲዳማ ክልል ጤና ቢሮ የይርጋዓለም ሆስፒታል ሕክምና ኮሌጅ በተገበራቸው የለውጥ ሥራዎች የግብዓት አቅርቦት ችግሮቹን በራስ አቅም መፍታት መቻሉን አስታወቀ ።

የኮሌጁ ጄኔራል ዳይሬክተር አቶ ተመስገን ሳርሚሶ እንዳሉት፤ ሆስፒታሉ የአገልግሎት ጥራቱን ለማረጋገጥ ዘርፈ ብዙ የለውጥ ሥራዎች እያከናወነ ይገኛል።

በለውጥ ሥራዎቹም ከዚህ በፊት የህክምና መገልገያ መሳሪያዎች ሲበላሹ ጠግኖ ወደ ሥራ ለማስገባት የነበረውን ችግር የቀየረ የባዮ ሜዲካል ኢንጂነሪንግ ማዕከል መክፈቱን አንስተዋል።

ማዕከሉ አዳዲስ ማሽኖች ሲመጡም አግባብነታቸውን የመፈተሸ ሥራ እንደሚያከናውን አብራርተዋል።


ተቋሙ ከሆስፒታሉ አልፎ ለአካባቢው ላሉ ሌሎች ተቋማት የተበላሹ ማሽኖቻቸውን የጥገና አገልግሎት፤ አዳዲሶቹን ደግሞ ገጥሞ ወደ ሥራ የማስገባትና በሰው ኃይል ስልጠና ድጋፍ እንደሚያደርግም ተናግረዋል።

ሆስፒታሉ የነበረበትን የኦክስጅን አቅርቦት ችግር ለመፍታት ኮሌጁ ያቋቋመው የኦክስጅን ማምረቻ ፋብሪካ በቅርቡ ሥራ መጀመሩን አስታውቀዋል።

ይህም ለኦክስጅን ግዢና ለትራንስፖርት ይወጣ የነበረን ከፍተኛ ወጪ መቀነስ እንዳስቻለው ገልጸዋል።

ፋብሪካው በቀን 192 ሲሊንደር ኦክስጅን በማምረት ከራሱ ፍጆታ አልፎ ለሌሎች ሆስፒታሎች እያቀረበ መሆኑን አስረድተዋል።


የማዕከሉ አስተባባሪና ሰርቪስ ኢንጂነር አቶ ወርቅነህ ሳሳሞ በበኩላቸው፤ ማዕከሉ ብልሽት የገጠማቸው የህክምናና የምርመራ መሳሪያዎችን እየጠገነ መሆኑን ገልጸዋል።

በተጨማሪም በሥራ ላይ ያሉትን የህክምና መሳሪያዎች ጥራት የመፈተሸ ሥራና የሥልጠና ማዕከል ሆኖ ማገልገሉንም ጠቁመዋል።

ለምርመራና ለህክምና መሳሪያዎች የሚደረገው ፍተሻ ታካሚው ጥራት ያለው የህክምና አገልግሎት እንዲያገኝ መሰረታዊ ነው ብለዋል።

በኦክስጅን ፋብሪካው የባዮ ሜዲካል ቴክኒሻን አቶ ሲሳይ ማሞ ፤ ፋብሪካው 24 ሰዓት ኦክሲጅን እንደሚያመርት ገልጸዋል።


የሚመረተው ኦክስጅን በሚፈለገው ጥራትና ልኬት ወደ ሲሊንደር መሞላቱን በማረጋገጥም ለሆስፒታሉና ለሌሎች ተቋማት እያቀረቡ እንደሚገኙ አስረድተዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.