የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

<p>በክልሉ የመሰረተ ልማት ሥራዎች ተጠናቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ እየተደረገ ያለው ድጋፍ መጠናከር አለበት--ሚኒስቴሩ</p>

Feb 18, 2025

IDOPRESS

ሀዋሳ፤ የካቲት 10/2017 (ኢዜአ)፡-በሲዳማ ክልል በግንባታ ላይ ያሉ የመሰረተ ልማት ሥራዎች ተጠናቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ እየተደረገ ያለው ድጋፍ የሚበረታታና መጠናከር እንዳለበት የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር ገለጸ።

የከተማ ልማት ሚንስቴር ድጋፋዊ ሱፐርቪዥን ቡድን በክልሉ በፌዴራል መንግስት የሚሰሩ የመንገድና ሌሎች መሰረተ ልማቶች ያሉበትን የአፈጻጸም ደረጃ ተመልክቷል።


በመስክ ምልከታ በፕሮጀክቶች አፈጻጸም ላይ የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ በተገኙበት ግብር መልስ ሰጥቷል።

የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዲኤታ አቶ የትምጌታ አሥራት የመሰረተ ልማት ግንባታ ሥራ የተለያዩ ባለድርሻዎችን ቅንጅታዊ ድጋፍና ክትትል እንደሚፈልግ ገልጸዋል።

በክልሉ በፌዴራል መንግስት የሚከናወኑ የመንገድና የከተማ መሰረተ ልማት ሥራዎች ላይ ምልከታ መደረጉንም ተናግረዋል።

በዚህም በፌዴራል መንግስት የሚገነቡ ዳዬ-ጭሬ፣ ዳዬ-ግርጃ እና የሀዌላ-ቱላ የአስፓልት መንገድ ፕሮጀክቶች እንዲሁም በሀዋሳና ይርጋለም ከተሞች የሚከናወኑ የኮሪደር ልማት ሥራዎችን ቡድኑ መመልከቱን ገልጸዋል።

በክልሉ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት እንዲበቁና የህብረተሰቡ ተጠቃሚነት እንዲረጋገጥ በአመራሩ እየተደረገ ያለው ክትትል የሚበረታታ መሆኑንም ተናግረዋል።

የኮሪደር ልማት ሥራ የከተሞችን የወደፊት እድገት ጭምር ታሳቢ አድርጎ እየተከናወነ መሆኑን በመስክ ምልከታ ወቅት መገንዘባቸውንም ተናግረዋል።

በሀዋሳ ከተማ የመጀመሪያው ምዕራፍ የኮሪደር ልማት ሥራ በጥሩ ሁኔታ መጠናቀቁን የገለጹት ሚኒስትር ዴኤታው፣ የሁለተኛው ምዕራፍ የኮሪደር ልማት እንቅስቃሴም ልማቱን ለማስፋፋት በመንግስት የተያዘውን አቅጣጫ እውን የሚያደርግ መሆኑንም ገልጸዋል።


በሲዳማ ክልል በፌዴራል መንግስት ድጋፍ ከ200 ኪሎ ሜትር በላይ ሦስት የአስፓልት መንገድ ፕሮጀክቶች ግንባታ እየተካሄደ መሆኑን የገለጹት ደግሞ በኢትዮጵያ መንገዶች አስተዳደር የደቡብ ሪጅን ዳይሬክተር ኢንጂነር ዳዊት ጥጋቡ ናቸው።

የግንባታው ሂደት በተለያየ ምክንያት ተቀዛቅዞ እንደነበር አስታውሰው፣ ሚኒስቴሩና የክልሉ መንግስት በሰጡት ትኩረት በአሁኑ ወቅት የግንባታው ሂደት በጥሩ ሁኔታ ላይ ይገኛል ብለዋል።

የመስክ ምልከታውና በፕሮጀክቶቹ ላይ ውይይት መደረጉ ትብብርን በማጠናከር የመንገድ ፕሮጀክቶቹን ፈጥኖ ለማጠናቀቅ እንደሚያግዝም ተናግረዋል።

የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ በበኩላቸው በክልሉ የሚከናወኑ መሰረተ ልማቶች ተጠናቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ የተናበበ ክትትል፣ ቁጥጥርና ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።


"ግንባታው እንዳይጠናቀቅ እንቅፋት የሆኑ የወሰን ማስከበርና መሰል ችግሮችን ከፌዴራል መንግስት ጋር በመቀናጀት እንዲፈቱና ስራው እንዳይቆም ለማድረግ የክልሉ መንግስት የበኩሉን ይወጣል።" ሲሉም ገልጸዋል።

ለዚህም ከክልል ጀምሮ አስከወረዳ ድረስ በቅንጅት ሲሰራ የነበረው በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመልክተዋል።

የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር ድጋፋዊ የሱፐርቪዥን ቡድን በክልሉ የሚከናወኑ መሰረተ ልማቶችን በጥልቀት በመፈተሽ ለሰጠው ግብረ መልስም አቶ ደስታ አመስግነዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.