ቁሊቶ፤ የካቲት 19/2017(ኢዜአ)፡- በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የህብረት ሥራ ማህበራትን በማዋሃድ የአባሎቻቸውንና የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ለማሳደግ እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ህብረት ሥራ ኤጀንሲ አስታወቀ፡፡
"የተዋሃዱ ህብረት ሥራ ዩኒየኖች ለሁለንተናዊ ብልፅግና" በሚል መሪ ሀሳብ የዩኒየኖች ውህደት መድረክ በክልሉ ሀላባ ዞን ቁሊቶ ከተማ ተካሂዷል፡፡
የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር አቶ ተመስገን ጎዴቦ እንደገለጹት፣ በክልሉ የህብረት ሥራ ማህበራት የአባሎቻቸውንና የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት በላቀ መልኩ እንዲያረጋግጡ የማዋሃድ ሥራ እየተሰራ ነው፡፡
በክልሉ ከ1 ነጥብ 1 ቢሊዮን በላይ ካፒታል ያስመዘገቡ ከ3 ሺህ 900 በላይ የህብረት ሥራ ማህበራት እንዳሉ ገልጸው፣ ማህበራቱ በተበጣጠሰ መንገድ ከሚሰሩ በማዋሃድ የበለጠ ተወዳዳሪና ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተደረገ ነው ብለዋል፡፡
መዋሃዳቸው አቅም በመፍጠር በአቅርቦት ላይ ያለውን ውስንነት ከመፍታት ባለፈ ምርቶችን እሴት ጨምረው በመላክ ለኢኮኖሚያዊ እድገት የበኩላቸውን እንዲጫወቱ ዕድል እንደሚፈጥርላቸው ገልጸዋል፡፡
የሀላባ ዞን ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና መምሪያ ኃላፊ አቶ ሀጂ ኑርዬ በበኩላቸው በዞኑ የአፈር ማዳበሪያና ምርጥ ዘር በማቅረብ የተደራጁ የህብረት ሥራ ማህበራት ውጤታማ እየሆኑ መምጣታቸውን ተናግረዋል፡፡
በተቃራኒው ከተነሱበት ዓላማ ውጪ በመንቀሳቀስ ለእዳ የተጋለጡ ህብረት ሥራ ማህበራት መኖራቸውን ጠቁመዋል፡፡
ውህደቱ የአባላትንም ሆነ የማህበረሰቡን ተጠቃሚነት ከማረጋገጥ ባለፈ ማህበራቱ በተሰማሩበ መስክ አቅማቸውን አሰባስበው ለለውጥ እንዲተጉ ያስችላቸዋል ብለዋል።
የህብረት ሥራ ማህበራቱ ውህደት ተወዳዳሪ የሆኑ የህብረት ሥራ ማህበራትን መፍጠር የሚያስችል ነው ያሉት ደግሞ የዞኑ ህብረት ሥራ ኤጀንሲ ፅህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ጀማል ኢብራሂም ናቸው።
በዛሬው ዕለትም ሁለት የህብረት ሥራ ማህበራት በአንድ ላይ መዋሃዳቸውን ጠቅሰው ውህደቱ የነበራቸውን ሀብት በማሳደግ የአካባቢውን ማህበረሰብ ተጠቃሚ ለማድረግ ያግዛቸዋል ብለዋል።
ማህበራቱ ሲዋሃዱ ሀብታቸው ከ24 ሚሊየን 450 ሺህ ብር በላይ መድረሱንም ጠቅሰዋል።
ከዚህ ቀደም ህብረት ሥራ ማህበሩ የአካባቢውን አርሶ አደሮች በተለያየ መንገድ በማገዝ በርካታ ተግባራትን ሲያከናውኑ መቆየታቸውን ያስታወሱት ደግሞ የሀላባ ማንቼኖ ህብረት ሥራ ዩኒየን ሥራ አስፈፃሚ አቶ ኑርአህመድ ሞሳ ናቸው፡፡
በዛሬው ዕለት ከሌላ አቻ ማህበር ጋር በመዋሃድ አንድ ጠንካራ ማህበር ሆነናል ያሉት ሥራ አስፈጻሚው፣ ውህደቱ ያፈሩትን ሀብት በጋራ በመጠቀም የተሻለ ሥራ ለመስራት እድል እንደሚፈጥርላቸው ተናግረዋል።
በመርሃ ግብሩ ላይ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክልሉ ገጠር ልማት ክላስተር አስተባባሪና የግብርና ቢሮ ሃላፊ አቶ ኡስማን ሱሩር ጨምሮ ሌሎች የክልልና የዞን የሥራ ሃላፊዎችና የህብረት ሥራ ማህበራት ተገኝተዋል፡፡
ቦንጋ ፤የካቲት 16/2017 (ኢዜአ) ፡-በቦንጋ ከተማ የተካሄደውን የህዝብ ውይይት የመሩ ከፍተኛ የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች በከተማው የተለያዩ የልማት ...
Feb 24, 2025
ደብረብርሀን፤ የካቲት 15/2017(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ገበያን ለማረጋጋት የሚያግዙ ከአንድ ነጥብ አንድ ቢሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የገበያ ማዕከላት ግንባታ...
Feb 24, 2025
አዲስ አበባ፤ የካቲት 1/2017(ኢዜአ)፡- በሚቀጥሉት አምስት አመታት በወረቀት የሚካሔዱ አሰራሮችን በማስቀረት የዲጂታል ቴክኖሎጂ ግብይትና አገልግሎት በተሻለ ...
Feb 8, 2025