የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ፖለቲካ እና ደህንነት

<p>የአድዋን ድል ጀግንነት በድህነት ላይ በመድገም አገራዊ ብልጽግናን ማረጋገጥ ይገባል</p>

Mar 3, 2025

IDOPRESS

አርባምንጭ፤የካቲት 23/2017ኢዜአ)፦የአድዋን ድል ጀግንነት በድህነት ላይ በመድገም አገራዊ ብልጽግናን ማረጋገጥ እንደሚገባ ተገለጸ።


129ኛው የአድዋ ድል በዓል በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ በፓናል ውይይት እየተከበረ ነው።


በፓናል ውይይቱ ላይም የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ አካዳሚክ ጉዳይ ምክትል ፕሬዚዳንትና የፕሬዚዳንቱ ተወካይ ኢንጂነር ቦጋለ ገብረማሪያም (ዶ/ር)፥ የጥንት አባቶቻችን በማበር የተቀዳጁት የአድዋ ድል ለጥቁር ህዝቦች ነፃነትን ማረጋገጡን አውስተዋል።


የአሁኑ ትውልድም የአድዋን ድል ጀግንነት በድህነት ላይ በመድገም አገራዊ ብልጽግናን ሊያረጋግጥ ይገባል ብለዋል።


በአባይ ወንዝ ጉዳይ ሀጋራዊ የጋራ ትርክት መገንባቱን ጠቅሰው፥ አንድነታችንን ይበልጥ በማጠናከር ድህነት ላይ ድል መቀዳጀት ይጠበቅብናል ሲሉ አመልክተዋል።


ከተባበርን የሀገር ሉዐላዊነትን ብቻ ሳይሆን የኢኮኖሚ ሉዐላዊነትን ማረጋገጥ እንደምንችል አድዋ ማሳያችን ነው ያሉት ምክትል ፕሬዚዳንቱ ታሪክ እየዘከርን ታሪክ በመፃፍ ለመጪው ትውልድ የተሻለች ሀገር የማውረስ ታሪካዊ ኃላፊነት አለብን ብለዋል።


ከአድዋ ድል አንድነት፣ቆራጥነትና ሀገር ወዳድነትን ልንማር ይገባል ያሉት ደግሞ የአርባምንጭ ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ትብብር ምክትል ፕሬዚዳንት ዶክተር ተክሉ ወጋየሁ ናቸው።


ልዩነቶቻችንን ወደ ጎን በመተው ችግሮቻችንን በውይይትና በምክክር መፍታት አለብን ሲሉም አክለዋል።


የጋሞ እና ጎፋ ዞኖች ጥንታዊ ኢትዮጵያ አርበኞች ማህበር ሊቀመንበር አቶ ተስፋዬ ገመዳ በበኩላቸው፥ የአድዋ ድል የህብርና የአንድነት ውጤት ነው ብለዋል።


ቀደምት አባቶቻችን ዘር፣ብሔር ፥የሃይማኖት ልዩነት ሳያግዳቸው ደማቸውን አፍሰውና አጥንታቸውን ከስክሰው ኢትዮጵያን አኑረዋል ነው ያሉት።


ኢትዮጵያን ከነ ሙሉ ክብሯ ለመጪው ትውልድ የማስተላለፍ አደራ አለብን ሲሉም አመልክተዋል።


በፓናል ውይይቱም "በኢትዮጵያ ሴቶች የጀግንነት ውሎ እና በዝክረ አድዋ አላማ" ላይ ያተኮሩ ሁለት ሰነዶች ቀርበው ውይይት እየተደረገባቸው ይገኛል።


በበዓሉ ላይም የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ማህበረሰብ፣ ጥንታዊት አርበኞች፣የሀገር ሽማግሌዎችና የሃይማኖት አባቶች ተገኝተዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.