የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ፖለቲካ እና ደህንነት

በክልሉ የህዝቡን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ለመመለስ የተጀመሩ ሥራዎች ሊጠናከሩ ይገባል

Mar 10, 2025

IDOPRESS

አርባምንጭ የካቲት 29/2017(ኢዜአ):- በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የህዝብን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ለመመለስ የተጀመሩ ሥራዎች ሊጠናከሩ እንደሚገባ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ገለጹ።

በክልሉ የ2017 ግማሽ ዓመት የፓርላማና የክልል ምክር ቤት አባላት ውክልና ሥራዎች አፈጻጸም ግምገማ መድረክ በአርባ ምንጭ ከተማ ተካሄዷል።


የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት በልማትና በመልካም አስተዳደር ጉዳዮች ዙሪያ ከመረጧቸው ህዝቦች ጋር ሰሞኑን ውይይት ሲያደርጉ የቆዩ ሲሆን በዛሬው ዕለት ደግሞ ከክልሉ አመራር አባላት ጋር የማጠቃለያ መድረክ አካሄደዋል።

በምክር ቤቱ የመንግስት ልማት ድርጅት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ ኢንጂነር ስለሺ ኮሬ (ዶ/ር) በክልሉ በፖለቲካ፣ በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች አበረታች ውጤቶች መመዝገባቸውን በመስክ ምልከታ ማረጋገጣቸውን ገልጸዋል።

በተለይ በፌደራልና በክልሉ መንግስት እየተከናወኑ የሚገኙ የጤና እና የትምህርት ልማቶች ህዝቡን ተጠቃሚ ማድረጋቸውን ጠቅሰዋል።

የግብርና ግብዓትና ቴክኖሎጂ አቅርቦት፣ የኑሮ ውድነትን ለማረጋጋት የተጀመሩ ተግባራትና የሀገር ውስጥና የውጭ የሥራ ዕድል ፈጠራዎችም እንዲጠናከሩ አሳስበዋል።


የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባልና የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የህዝብ ውክልና ሥራ አስተባባሪ አቶ መለሰ መና በበኩላቸው ከመንግስት ሠራተኞች የወርሃዊ ደመወዝ ክፍያ ጋር የሚነሱ ቅሬታዎች እየተፈቱ መምጣታቸውን መገንዘባቸውን ተናግረዋል።

''የህዝብ የመልማት ጥያቄ ከሆኑት ጉዳዮች መካከል ለተጓተቱ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች ምላሽ ለመስጠት እየተደረጉ ያሉ ጥረቶች ሊጠናከሩ ይገባል'' ብለዋል።

በተለይም የመንገድ፣ የንጹህ መጠጥ ውሃ እና የመብራት አገልግሎት ልማት ሥራዎችን በፍትሃዊነት ተደራሽ ከማድረግ አንጻር ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ እንዳለም ጠቁመዋል።

በተጨማሪም የመንግስት ተቋማት የአገልግሎት አሰጣጥ ሂደት ተጠያቂነት ባለውና ፍትሃዊ በሆነ መንገድ እንዲከናወን እንዲሁም የነዳጅ አቅርቦት ችግርና ህገ-ወጥነትን የማስወገዱ ተግባር በትኩረት ሊሠራ ይገባል ብለዋል።


የተሰጡ አስተያየቶች በመቀበል በቀጣይ በሁሉም መስክ የላቀ አፈጻጸም ለማስመዝገብ ይሰራል ያሉት ደግሞ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ተወካይ ዶክተር ቦሼ ቦምቤ ናቸው

በተለይም የግብርና ግብአት አቅርቦትና ሜካናይዜሽንን በማስፋፋት፣ ምርትና ምርታማነትን በመጨመር፣ የኑሮ ውድነት ለመቅረፍ የተጀመሩ ውጤታማ ጥረቶች ይጠናከራሉ ብለዋል።

የጤና ተቋማት ግንባታ በማፋጠን አገልግሎቱን ለማሳለጥ እንዲሁም የትምህርት ጥራት ለማስጠበቅ ህዝቡን ያሳተፈ ንቅናቄ በመፈጠሩ ለውጥ እየተመዘገበ ይገኛል ብለዋል።

በክልሉ ባሉ 12 ዞኖች ከህዝቡ የሚነሱ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ለመመለስ በትኩረት እንደሚሠራም ዶክተር ቦሼ ጠቁመዋል።

ለአንድ ቀን በተዘጋጀው መድረክ የክልሉ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ የክልል ምክር ቤት አባላት፣ የክልሉ አስፈጻሚ አካላት እና የዞን አፈ-ጉባኤዎች ተሳትፈዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.