የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ፖለቲካ እና ደህንነት

የፈጠራ ውጤቶቻችን ተኪ ምርቶችን በማምረት የውጭ ምንዛሬን ለማዳን የሚያግዙ ናቸው

Mar 18, 2025

IDOPRESS

መቀሌ፤መጋቢት 8/2017(ኢዜአ)፦የፈጠራና የምርምር ውጤቶቻችን ተኪ ምርቶችን በማምረት የውጭ ምንዛሬን ለማዳን የሚያግዙ ናቸው ሲሉ በትግራይ ክልል የአዕምሯዊ ንብረት የባለቤትነት ሰርተፊኬት የተሰጣቸው የፈጠራ ባለቤቶች ገለጹ።


በትግራይ ክልል በበጀት ዓመቱ ስምንት ወራት 55 ለሚሆኑ የፈጠራና የምርምር ውጤቶች የአዕምሯዊ ንብረት የባለቤትነት እውቅናና ማረጋገጫ ሰርተፊኬት መሰጠቱም ተገልጿል።


በትግራይ ክልል የአዕምሯዊ ንብረት የባለቤትነት ሰርተፊኬት የተሰጣቸው የፈጠራ ባለቤቶች፤የፈጠራና የምርምር ውጤቶቻቸው ተኪ ምርቶችን በማምረት የውጭ ምንዛሬን ለማዳን የሚያግዙ መሆናቸውን ገልጸዋል።


የፈጠራና የምርምር ውጤቶቹን ወደ ተግባር በመቀየር የስራ ዕድል ለመፍጠር በማቀድ እየተንቀሳቀሱ መሆኑንም ተናግረዋል።


ከሰባት የምርምር ዓመታት በኋላ እውቅና እንደተሰጣቸው የገለፁት የኮምፖስት (የተፈጥሮ ማዳበሪያ) ተማራማሪው ካህሳይ ሃይለ ኪሮስ (ዶ/ር)፤ ደረቅ ቆሻሻና አረምን አብላልቶ ወደ ኮምፖስት የሚቀይር የፈጠራ ስራ ማፍለቃቸውን ገልፀዋል።


የግብርና ልማትን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግም ከባለሃብት ጋር በሽርክና ከ250 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ የኮምፖስት ማቀነባበሪያ ፋብሪካ በአዲስ አበባ ቃሊቲ አካባቢ እያቋቋሙ መሆኑን አስረድተዋል።


በደብረ ታቦር ዩኒቨርሲቲ በኤሌክትሪካል እና ኮምፒዩተር ኢንጂነሪንግ እንደተመረቀች የገለፀችው ወጣቷ ተማራማሪ ሜሪን ወልደ ስላሴ፤ ከፈጠራ ውጤቶቿ ምርቶች መካከል የመሬት ወለል ንጣፍ፣ግድግዳ ላይ የሚሰቀሉ ጌጦች፣ለምግብና መጠጥ የሚያገለግሉ ዕቃዎች እንዲሁም ልዩ ልዩ ጌጣጌጦችን ለአብነት ጠቅሳለች።


በቀጣይ ዓመት ያላትን ዕውቀት ለሌሎች ለማካፈል የስልጠና ማዕከል ለመክፈት እቅድ እንዳላት ገልፃለች።


የበለስ ተክልን በማጥፋት ላይ የሚገኝ ''ኮችንያል'' የተባለ ተባይን የሚያጠፋ ፈሳሽ መድኃኒት በምርምር በማግኘት የአዕምሮአዊ ንብረት ማረጋገጫ ባለቤትነት ሰርተፊኬት እንደተሰጣቸው የገለፁት ደግሞ አቶ ጎይቶም ገብረፃድቅ ናቸው።


በትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር የኢኖቬሽን ሳይንስና ቴክኖሎጂ ቢሮ የአዕምሯዊ ንብረት ምዝገባ ዳሬክተር አቶ ገብረፃድቅ ተስፋይ፤በበጀት ዓመቱ ስምንት ወራት ለቢሮው ከቀረቡ 59 የምርምርና ፈጠራ ውጤቶች መካከል ለ55ቱ የባለቤትነት ማረጋገጫ እውቅና ተሰጥቷል ብለዋል።


የምርምር እና የፈጠራ ውጤቶቹም ችግር ፈቺ ስለመሆናቸው በሙከራ ፍተሻ የተደረገባቸው እንደሆኑም ተናግረዋል።


በተጨማሪም የምርምር ውጤቶቹ በውጭ ምንዛሪ የሚገዙ ምርቶችን በአገር ውስጥ ለመተካትና ሌሎች ችግሮችን ለመፍታት እንደሚያስችሉ የታመነባቸው ናቸው ብለዋል።


የፈጠራ እና ምርምር ሥራዎቹ በግብርና፣በማኑፋክቸሪንግ፣ በኮንስትራክሽን፣በአግሮ ፕሮሰሲንግ፣በጤና እና ሌሎች ዘርፎች ላይ ያተኮሩ መሆናቸውንም ገልፀዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.