የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ፖለቲካ እና ደህንነት

በክልሉ የግብርናውን ልማት በማጠናከር የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ ጠንክሮ መስራት ይገባል - ርዕሰ መስተዳድር አለሚቱ ኡሞድ

Apr 10, 2025

IDOPRESS

ጋምቤላ ፤ሚያዝያ 1/2017 (ኢዜአ)፡- በጋምቤላ ክልል የግብርናውን ልማት በማጠናከር የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥና ከተረጂነት ለመላቀቅ ጠንክሮ መስራት ይገባል ሲሉ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ወይዘሮ አለሚቱ ኡሞድ ገለፁ።

የክልሉ የግብርና ልማት አጋር አካላት ግንኙነት አማካሪ ካውንስል የ2017 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ዙር ጠቅላላ ጉባዔውን ዛሬ በጋምቤላ ከተማ አካሂዷል ።


ርዕሰ መስተዳድሯ በጉባዔው ላይ ተገኝተው አንዳሉት "ከድህነትና ከተረጂነት ለመላቀቅ ልዩ ትኩረት ከተሰጣቸው ዘርፎች መካከል ግብርና ቀዳሚውን ድርሻ ይይዛል"።

ክልሉ በዝናብና በመስኖ ሊለማ የሚችል ሰፊ የመሬትና የውሃ ሀብት ያለው ቢሆንም ቀደም ሲል ለዘርፉ የተሰጠው ትኩረት አናሳ ከመሆኑ የተነሳ የሚፈለገው ውጤት ሳይገኝ መቆየቱን አክለዋል።

በተለይም ዘርፉ በተሟላ የግብርና ግብዓት፣ የኤክስቴንሽን አገልግሎትና በግብርና ቴክኖሎጂዎች ባለመደገፉ ምርትና ምርታማነትማሳደግ ላይ ተግዳሮት ሆኖ መቆየቱን አውስተዋል።

በመሆኑም የግብርናውን ልማት የሚያሳልጡ ግብዓቶችንና ቴክኖሎጂዎችን ተደራሽ በማድረግ ምርትና ምርታማነትን በማሳደግ ከተረጂነት ለመላቀቅ ተግተን ልንሰራ ይገባል ብለዋል።

ችግር ፈቺ ምርምሮችን በማድረግና ውጤታማ የሆኑ ቴክኖሎጂዎችን በማፍለቅ የአርሶና አርብቶ አደሩን ምርታማነት በማሻሻል ረገድ ከዘርፉ ባለድርሻ አካላት የላቀ ሚና እንደሚጠበቅም አሳስበዋል።

የግብርና ልማት አማካሪ ካውንስሉ ዋና ዓላማም የአርሶና ከፊል አርብቶ አደሩን ምርትና ምርታማነት በማሳደግ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ በሚከናወኑት ተግባራት የራሱን እገዛ እንዲያደርግ መሆኑን ገልፀዋል።


የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሃብት ልማት ቢሮ ኃላፊ አቶ ፓል ቱት በበኩላቸው እንዳሉት በክልሉ የግብርና ኤክስቴንሽን አገልግሎቱን በማሳለጥ የአርሶና አርብቶ አደሩን ምርታማነት ለማሳደግ እየተሰራ ይገኛል።

በተለይም በምርምር ውጤታማ የሆኑ የግብርና ግብዓቶችን ለአርሶና አርብቶ አደሩ ተደራሽ ለማድረግ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

በግብርናው ዘርፍ የሚስተዋሉ የግብርና ቴክኖሎጂና የግብዓት አቅርቦትም በቢሮው ጥረት ብቻ ውጤታማ ማድረግ እንደማይቻል ጠቅሰው ለዘርፉ ስኬታማነት የአጋር አካላት ተሳትፎ ሊጠናከር ይገባል ብለዋል።

ለግማሽ ቀን በተካሄደው የክልሉ ግብርና አማካሪ ካውንስል ጠቅላላ ጉባዔ ላይ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ የዘርፉ ባለድርሻ አካላት ተገኝተዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.