የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

ኢትዮጵያ በአፍሪካ እድገት ውስጥ ቁልፍ ሚና ያላት ስትራቴጂካዊ ሀገር ናት- አፍሪኤግዚም ባንክ

Apr 11, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ ሚያዚያ 2/2017 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በአፍሪካ እድገት ውስጥ ቁልፍ ሚና ያላት ስትራቴጂካዊ ሀገር መሆኗን የአፍሪካ ኢምፖርትና ኤክስፖርት ባንክ (አፍሪኤግዚም) የህግ ተገዢነት ዳይሬክተር ኢድሪሳ ዲዮፕ ገለጹ።

ዳይሬክተሩ ከኢዜአ ጋር በነበራቸው ቆይታ ኢትዮጵያ ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት በየዓመቱ ሀገራዊ ጥቅል ምርቷ (ጂዲፒ) እድገት እንዳስመዘገበ ማየታቸውን አውስተዋል።

በቅርብ ጊዜ የተደረጉ የህግ እና የአሰራር ማዕቀፍ ለውጦች በኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ላይ በጎ ተጽእኖ ማሳደራቸውን አመልክተዋል።

የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ በውጭ ምንዛሬ ላይ ተግባራዊ ማድረግ የጀመረው ፖሊሲ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ለመሳብ እና የውጭ ምንዛሬ ክምችትን ለመጨመር አስተዋጽኦ ማድረጉን ተናግረዋል።

የህግ ማዕቀፎቹ ኢትዮጵያን ለውጭ ገበያ ክፍት እንድትሆንና ዓለም አቀፍ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ የሚያስችል ሁኔታ መፍጠሯ በጎ ተግባር መሆኑን ጠቅሰዋል።

የማሻሻያ ስራው የአፍሪኤግዚም ባንክ ትኩረትን መሳቡን የገለጹት ዳይሬክተሩ ኢትዮጵያ ለባንኩ ቁልፍ የገበያ መዳረሻ እንደሆነች ተናግረዋል።

ባንኩ በኢትዮጵያ የቢዝነስ ስራዎች እና የፋይናንስ ተቋማትን እየደገፈ እንደሚገኝም አመልክተዋል።

አፍሪኤግዚም ባንክ በፋይናንስ ክፍያ ስርዓቱ አማካኝነት ድንበር ዘለል የንግድ ልውውጥን የመደገፍ ፍላጎት እንዳለውም ነው ዳይሬክተሩ የጠቆሙት።

የክፍያ ስርዓቱ ለግዙፍ ኩባንያዎችም የንግድ ፋይናንስ እና የብድር ማዕቀፍ ማቅረብን ጨምሮ የተለያዩ ድጋፎች ለአፍሪካ ሀገራት እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል።

ባንኩ ከኢትዮጵያ ጋር በአጋርነት በመስራት ለኢትዮጵያ የኢኮኖሚ እድገት ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑን አመልክተዋል።

በኢትዮጵያ ላይ ስትራቴጂካዊ ትኩረቱን በማድረግ ለሀገሪቷ ዘላቂ እድገት በትብብር እንደሚሰራም አክለዋል።

እ.አ.አ በ1993 የተቋቋመው አፍሪኤግዚም ባንክ ለአፍሪካ ሀገራት መንግስታትና የግሉ ዘርፍ የፋይናንስ አቅርቦት በመስጠት የአፍሪካ የንግድ አቅምና ልውውጥ እንዲያድግ የሚሰራ የፋይናንስ ተቋም ነው።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.