የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

በ63 ከተሞች የኮሪደር ልማት እየተከናወነ ነው- ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ

Apr 15, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 6/2017(ኢዜአ)፦ በአዲስ አበባ የተጀመረው የኮሪደር ልማት አሁን ላይ በ63 ከተሞች እየተከናወነ መሆኑን የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ገለጹ።

በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነትና አመራር ሰጪነት በርካታ ከተሞች ጽዱና ምቹ የመኖሪያና የማምረቻ ማዕከል እየሆኑ እንደሚገኙም ተናግረዋል።

ሚኒስትሯ ባለፉት ዘጠኝ ወራት በከተማና መሰረተ ልማት ዘርፍ በተከናወኑ ተግባራት አመርቂ ውጤቶች መመዝገባቸውን አንስተዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ለሁሉም ዘርፎች እየሰጡ ባሉት የአመራር ድጋፍና ክትትል እንዲሁም በሕዝቡ ተሳትፎ ከዕቅድ በላይ አፈጻጸም መኖሩንም ነው የገለጹት።

ይህ ዘመን የከተሞች የህዳሴ ዘመን ነው ያሉት ሚኒስትሯ የኮሪደር ልማቱ የበርካታ ከተሞችን መሠረተ ልማት በማሻሻል አካታች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን እያረጋገጠ ነው ብለዋል።

በአዲስ አበባ የተገኘውን ተሞክሮውን በማስፋት በአሁኑ ወቅት በ63 ከተሞች የኮሪደር ልማቱ እየተተገበረ እንደሚገኝም ጠቅሰዋል።

በዚህም በብዙ ከተሞች የተጎሳቆሉና በአረንቋ ውስጥ የቆዩ ሰፈሮች ሙሉ ለሙሉ ተቀይረው ዘመናዊ፣ ውብና ምቹ የመኖሪያ፣ የሥራና የመዝናኛ ማዕከል እየሆኑ ነው ብለዋል።

በኮሪደር ልማቱ የተሽከርካሪ፣ የእግረኛና የብስክሌት መንገድ፣ የመብራትና ሌሎችም የአገልግሎት መሰረተ ልማቶች በስፋት ተገንብተው ህዝቡን ተጠቃሚ እያደረጉ መሆኑን አንስተዋል።

ይህም መንግሥት በሁሉም አካባቢ ፍትሐዊ ልማትን ተደራሽ ለማድረግ የጀመረውን ጉዞ የሚያሳካ ነው ብለዋል።

ሚኒስትሯ አክለውም ከለውጡ በፊት 74 በመቶ የከተሞች ክፍል ደረጃውን ያልጠበቀና የተጎሳቆለ እንደነበር በማውሳት ከለውጡ ወዲህ በተከናወኑ የኮሪደር ልማትና ሌሎች ሥራዎች መሻሻል መጥቷል ነው ያሉት።

የኮሪደር ልማቱ ከተሞችን የፈጠራ፣ የምርምር፣ የአዳዲስ ሀሳቦች መፍለቂያ እንዲሆኑ ከማድረጉም በላይ ከሸማችነት ወደ አምራችነት እንዲሸጋገሩ ዕድል መፍጠሩንም አንስተዋል።

የከተማ የአረንጓዴ ሽፋንም 5 በመቶ ከነበረበት ወደ 22 በመቶ ከፍ ማለቱን አስረድተዋል።

ሚኒስትሯ አያይዘው እንደገለጹት ከኮሪደር ልማት ባሻገር በሁሉም የሀገሪቱ አካባቢዎች የመሰረተ ልማት ግንባታዎች እየተፋጠኑ ነው ብለዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.