የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው የሀገር ውስጥ ኢንዱስትሪ ምርቶችን ተወዳዳሪነት አሳድጓል-አምባሳደር ግርማ ብሩ

May 6, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 27/2017(ኢዜአ)፦የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው የሀገር ውስጥ ኢንዱስትሪ ምርቶች ተወዳዳሪነት እንዲጨምር ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማክሮ ኢኮኖሚ አማካሪ አምባሳደር ግርማ ብሩ ገለጹ።


ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) 3ኛውን የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል በይፋ መክፈታቸው ይታወቃል።


የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማክሮ ኢኮኖሚ አማካሪ አምባሳደር ግርማ ብሩ እና የኮሙዩኒኬሽን ሚኒስትሩ ለገሰ ቱሉ (ዶ/ር) እንዲሁም የሚኒስቴሩ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ኤክስፖውን ጎብኝተዋል።


ጉብኝቱን አስመልክቶ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የማክሮ ኢኮኖሚ አማካሪ አምባሳደር ግርማ ብሩ በሰጡት ማብራሪያ፥ ኢትዮጵያ ታምርት የሀገር ውስጥ ምርታማነት እንዲጨምር ምቹ ሁኔታን ፈጥሯል ብለዋል።


የኢንዱስትሪ ዘርፉ የሚያስገኘውን ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ ለማጉላት በመንግስት እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ውጤት እያመጡ መሆናቸውን በኤክስፖው መመልከታቸውንም ተናግረዋል።


ዘርፉ ያለበትን የፋይናንስና መሰል ችግሮችን በመቅረፍ ረገድ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱንም አክለዋል።


የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው በዋናነት ትኩረት ካደረገባቸው ዘርፎች መካከል የኢንዱስትሪ ምርታማነትን መጨመር አንዱ መሆኑን ያብራሩት አማካሪው፥ በዚህም አበረታች ውጤት መመዝገብ ተችሏል ነው ያሉት።


ሀገር ውስጥ ኢንዱስትሪ ምርቶችን ተወዳዳሪነት ማሳደጉንም አንስተዋል።


የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስትር ዴኤታ ተስፋሁን ጎበዛይ በበኩላቸው፥ የኢትዮጵያ ታምርት ንቅናቄ የኢንዱስትሪ ዘርፉ ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር ማድረጉን አብራርተዋል።


በተጨማሪም ሀገሪቱ ያላትን እምቅ ሃብት ወደ ጥቅም የመቀየር ልምድ እየዳበረ መምጣቱን ገልጸው፥ ይህም የንቅናቄውን ውጤታማነት የሚያረጋግጥ ነው ብለዋል።


ንቅናቄው የታለመለትን ግብ እንዲመታ የመገናኛ ብዙሃን አስተዋጽኦ ጉልህ መሆኑንም ሚኒስትር ዴኤታው ገልጸዋል።


በመሆኑም ዘርፉን በማስተዋወቅና የተደራሽነት አድማሱን በማስፋት ሚናቸውን አጠናክረው መቀጠል እንደሚገባቸው አጽንኦት ሰጥተዋል።


ለአምስት ቀናት በሚካሄደው የኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ 288 ኢንዱስትሪዎች እየተሳተፉ ሲሆን፤ ከአራት ቢሊዮን ብር በላይ ግብይት ይፈፀማል ተብሎ ይጠበቃል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.