የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

የክልሉን ህዝብ የልማት ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ ምላሽ የመስጠት ስራ በተጠናከረ መልኩ ቀጥሏል - ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ

May 8, 2025

IDOPRESS

ጎንደር፤ ሚያዝያ 29/2017(ኢዜአ)፦ የአማራ ክልልን ህዝብ የልማት ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ ምላሽ በመስጠት በኩል በቁርጠኝነት እየተሰራ መሆኑን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አረጋ ከበደ ገለጹ።

ርዕሰ መስተዳድሩ በጎንደር የመገጭ የመስኖና የመጠጥ ውሃ ግድብ ፕሮጀከት ግንባታ ሂደትን ተመልክተዋል።

ለበርካታ አመታት ተጓትቶ የቆየውን የመገጭ የመስኖና የመጠጥ ውሃ ግድብ ፕሮጀክት ግንባታ በማፋጠን ጥቅም ላይ ለማዋል ያለእረፍት በመሰራት ላይ መሆኑ ለዚሁ ጥሩ ማሳያ ነው ብለዋል።


የግድብ ግንባታው ለበርካታ ዓመታት ሲጓተት የቆየና ለመቆም ተቃርቦ እንደነበረ ጠቁመው ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በሰጡት አመራር አሁን ላይ የግንባታ ስራው በጥሩ አፈፃፀም ላይ መሆኑን ገልጸዋል።

የግድቡ ግንባታ በከፍተኛ ፍጥነትና ጥራት እየተከናወነ መሆኑን ገልጸው ፕሮጀክቱ ሲጠናቀቅ የጎንደር ከተማ የመጠጥ ውሃ ችግርን በዘላቂነት እንደሚፈታ ተናግረዋል።

በዚህም የክልሉ አመራር የህዝቡን የልማት ጥያቄዎች ደረጃ በደረጃ ምላሽ በመስጠት በኩል በቁርጠኝነት እየሠራ መሆኑን ገልጸዋል።

በአካባቢው የሰፈነው ሠላም ግድቡን በተያዘለት ጊዜ ለማጠናቀቅ ምቹ ሁኔታ መፍጠሩንም ጨምረው ተናግረዋል።


የፌዴራል መንግስትና ክልሉ ለግድብ ስራው የሚያስፈልጉ ግብዓቶችን ከማቅረብ ጀምሮ የግንባታው ተቋራጭ ስራውን በፍጥነት እንዲያጠናቅቅ የቅርብ ድጋፍና ክትትል እያደረጉ ነው ብለዋል።

በክልሉ እየተከናወኑ የሚገኙትን ግዙፍ የመሠረተ ልማት ስራዎች ፍጻሜ ላይ ለማድረስ ሠላም ወሳኝ መሆኑን ጠቁመው ህዝቡ ለሠላሙ አጥብቆ እንዲሰራም አሳስበዋል።

የመገጭ ግድብ 17 ሺህ ሄክታር መሬትን በመስኖ የማልማት አቅም ሲኖረው ከሚይዘው ውሃም 30 በመቶው ለጎንደር ከተማ የመጠጥ ውሃ አገልግሎት እንደሚውልም ታውቋል።

ግድቡ 185 ሚሊዮን ሜትር ኪዩብ ውሃ የመያዝ አቅም ሲኖረው 77 ሜትር ከፍታና 890 ሜትር ደግሞ የጎን ርዝመት እንዳለውም ለማወቅ ተችሏል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.