የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

በሲዳማ ክልል ለቡና አልሚ አርሶ አደሮች የምርት ማሳደጊያ ድጋፍ እየተደረገ ነው

May 12, 2025

IDOPRESS

ግንቦት 2/2017(ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል ለቡና አልሚ አርሶ አደሮች የምርት ማሳደጊያ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን የክልሉ እርሻና ተፈጥሮ ሀብት ልማት ቢሮ አስታውቋል።

የቢሮው ኃላፊ አቶ መምሩ ሞኬ ለኢዜአ እንዳሉት የአርሶ አደሩን ምርታማነት ለማሳደግ የተፈጥሮ ማዳበሪያ አቅርቦትን ጨምሮ ሌሎችም ድጋፎች እየተደረጉ ነው።

የተፈጥሮ ማዳበሪያ በተለይ ለእጽዋት እድገትና ጤናማነት የሚያስፈልጉ ንጥር ነገሮችን የያዘ በመሆኑ ለምርትና ምርታማነት እድገት ጉልህ አስተዋጽኦ አለው ብለዋል።

ይህንን ተሳቢ በማድረግም ቨርሚ ኮምፖስትና የተፈጥሮ ማዳበሪያን በስፋት አዘጋጅቶ ጥቅም ላይ ለማዋል በየደረጃው ጥረት እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል።


በክልሉ የሚገኙ 172 የቡና መፈልፈያ ኢንዱስትሪዎች ተለይተው 138ቱ የቨርሚ ኮምፖስት ማበልጸጊያ ማዕከል ግንባታ እንዲያካሄዱ በማድረግ ምርቱን ለቡና አልሚ አርሶ አደሮች እንዲደርስ እየተደረገ ነው ብለዋል።

በተሰራው ስራም በክልሉ የቡና ምርታማነት በሔክታር 9 ነጥብ 6 ከነበረበት ወደ 11 ነጥብ 4 ኩንታል ለማሳደግ መታቀዱንም ገልጸዋል።

በበጀት ዓመቱ በአካባቢው ከሚገኙ ተፈጥሮዊ ከሆኑ ቁሶች 4 ሚሊዮን ቶን የተፈጥሮ ማዳበሪያ ለማዘጋጀት ታቅዶ እስከ አሁን 4 ነጥብ 2 ሚሊዮን ቶን ማዘጋጀት መቻሉንም ተናግረዋል።

የተዘጋጀውን የተፈጥሮ ማዳበሪያ አርሶ አደሩ ለዘንድሮ መስኖና በልግ እርሻ በስፋት ጥቅም ላይ እያዋለው እንደሚገኝ አብራርተዋል።

በሌላ በኩል በአቅርቦት ረገድም እስከ አሁን ወደ ክልሉ ከገባው 150 ሺህ ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ውስጥ 87 በመቶ የሚሆነው ለዘንድሮ በልግ ወቅት መሰራጨቱን አመላክተዋል።


በክልሉ ዘንድሮ በበልግ እርሻው በዋና ዋና ሰብሎች ለማልማት በእቅድ ከተያዘው 72 ሺህ ሄክታር መሬት ውስጥ እስከ አሁን 68 ሺህ ሔክታር መሬት በዘር መሸፈን መቻሉን አቶ መምሩ አብራርተዋል።

በበልግ ወቅት በዘር ከተሸፈነው መሬት ውስጥ በቆሎ፣ ድንች እና ቦሎቄን ጨምሮ 91 በመቶ ምርጥ ዘር ጥቅም ላይ መዋሉንም አስረድተዋል።

በክልሉ የአፈር አሲዳማነት በምርታማነት ላይ ተጽእኖ እንዳያስከትልም መንግሥት በሰጠው ትኩረት 70 ሺህ ኩንታል ኖራ ለአርሶ አደሩ መሰራጨቱን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.