
አዲስ አበባ፤ ግንቦት 5/2017(ኢዜአ)፦ በሀገሪቱ ባለው እምቅ የእንስሳትና ዓሳ ሃብት ተጠቃሚነትን ለማሳደግ የግል ባለሃብቱ የኢንቨስትመንት ተሳትፎ መጎልበት እንዳለበት የግብርና ሚኒስቴር ገለጸ።
በኢትዮጵያ በእንስሳትና ዓሳ ሀብት ባሉ እምቅ የኢንቨስትመንት አማራጮች የግል ባለሀብቱ በስፋት ቢሰማራ ተጠቃሚ እንደሚሆንም ነው ሚኒስቴሩ ያመላከተው፡፡

ግብርና ሚኒስቴር ከዓለም አቀፍ እንስሳት ምርምር ኢንስቲትዩትና ከዓለም ዓቀፍ የግብርና ጥናት አማካሪ ግሩፕ ጋር በመቀናጀት በኢትዮጵያ እንስሳትና ዓሳ ሃብት ኢንቨስትመንት ላይ ያተኮረ መጽሐፍን የማስተዋወቅ መርሃ ግብር ተካሂዷል፡፡
የግብርና ሚኒስትር ዴኤታ ሶፊያ ካሳ(ዶ/ር) በዚሁ ወቅት፤ እንዳሉት ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀዳሚ የሆነ እምቅ የእንስሳትና ዓሳ ሃብት ባለቤት ነች፡፡
የእንስሳትና ዓሳ ሃብት የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ፣ የውጭ ምንዛሬ ግኝትን ለማስፋት፣ ለግብርና ስራና ለኢንቨስትመንት ከፍተኛ ፋይዳ እንዳለው ተናግረዋል።
በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ሀሳብ አመንጪነት ተግባራዊ እየተደረገ ያለው የሌማት ትሩፋት መርሃ ግብር የዜጎችን ተጠቃሚነት እያረጋገጠ እንደሚገኝም አመላክተዋል፡፡
በሀገሪቱ እምቅ የእንስሳትና ዓሳ ሃብት ቢኖርም ከዘርፉ የሚገኘው ጥቅም አነስተኛ መሆኑን ጠቅሰው፤ በቀጣይ ይህን ለማሳደግ የግል ባለሃብቱ የኢንቨስትመንት ተሳትፎ መጎልበት እንዳለበት ነው የገለጹት።
በኢትዮጵያ በእንስሳትና ዓሳ ሃብት ዘርፍ ያለውን የኢንቨስትመንት አቅምና አማራጮችን ላይ ያተኮረ መጽሐፍ መዘጋጀቱ የባለሃብቱን ግንዛቤ ለማጎልበት እንደሚያግዝም ተናግረዋል።
በግብርና ሚኒስቴር የእንስሳትና ዓሳ ኢንቨስትመንትና ምርት ግብይት ዴስክ ኃላፊ ከድር ሉባንጎ በበከላቸው፤ መጽሐፉ ኢትዮጵያ በመኖ ምርት፣ በማር፣ በዓሳ እና በተለያዩ እንስሳት ሀብቶች ያላትን ፀጋዎች በሙሉ ያካተተ ነው ብለዋል፡፡
በኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የሆለታ ግብርና ምርምር ማዕከል የእንስሳት ዝሪያ ማሻሻያ ተመራማሪ ዶክተር ተመስገን ጀምበር፤ በመጽሐፉ ዝግጅት ላይ መሳተፋቸውን ገልጸው፤ በመጽሐፉ ውስጥ የተለያዩ ሀገራትን ተሞክሮ በመቀመር ለኢትዮጵያ በሚመች መልኩ ማዘጋጀቱን ተናግረዋል፡፡
ከዚህ ቀደም በኢትዮጵያ ያለው የእንስሳት ምርትና እርባታ በአርሶና አርብቶ አደሩ ላይ ብቻ የተመሰረተ መሆኑን አስታውሰው፤ መጽሐፉ ባለሀብቶች በዘርፉ ባሉ ምቹ ዕድሎች ዙሪያ መረጃዎችን እንዲያገኙና እንዲሳተፉ የሚያግዝ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
የኢትዮጵያ ስጋ አምራችና ላኪዎች ማህበር ፕሬዝዳንት ከሊፋ ሁሴን በበኩላቸው የማህበሩ አባላቶች ስጋን ወደ ውጭ በመላክ ሀገሪቱ ከስጋ ምርት ማግኘት የሚገባትን የውጭ ምንዛሬ እንድታገኝ እየሰሩ መሆናቸውን ተናግረዋል።
ሆኖም ግን አልፎ አልፎ እንስሳት አቅርቦት ችግር መኖሩን ጠቅሰው አሁን የተዘጋጀው መጽሐፍ በዘርፉ ያሉትን ክፍተቶች በመፍታት በኩል አስተዋጽኦ ይኖረዋል ብለዋል፡፡
እንደ ግልም ሆነ እንደ ማህበር በእንስሳት እርባታ ዘርፍ ለመሰማራት ማቀዳቸውንም ጠቁመዋል፡፡
ሆሳዕና ፤ ነሐሴ 21/2018 (ኢዜአ) ፦ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች የህዝብ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚጠበቅባቸውን ሚና እንዲወጡ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ...
Aug 28, 2026
መቱ፤ ነሐሴ 11/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በኢሉባቦር ዞን በክረምት እርሻ እየለማ ከሚገኘው የበቆሎ ሰብል የላቀ ምርት ለማገኘት የሰብል እንክብካቤና ጥ...
Aug 18, 2026
ሀዋሳ፤ ነሐሴ 2/2018 (ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል የመንገድና ሌሎች መሰረተ ልማትን በማሻሻል ለሕዝቡ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆና...
Aug 10, 2026
አዳማ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል በበጀት ዓመቱ ሰላምና መልካም አስተዳደርን ከማረጋገጥ ጎን ለጎን ውጤታማ የልማት ሥራዎች መከናወናቸውን የክል...
Jul 20, 2026