የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

ኢትዮጵያ የዲጂታል መታወቂያ ልምዷን የምታካፍልበት አይዲ 4 አፍሪካ ጉባኤን ከነገ ጀምሮ ታስተናግዳለች

May 21, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ ግንቦት 11/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ የዲጂታል መታወቂያ ልምዷን የምታካፍልበት አይዲ 4 አፍሪካ ጉባኤን ከነገ ጀምሮ በአዲስ አበባ እንደምታስተናግድ የብሄራዊ መታወቂያ ፕሮግራም አስታወቀ።


ከ100 በላይ ሀገራት የሚሳተፉበት አይዲ 4 አፍሪካ ጉባኤ በዲጂታል ማንነት ላይ የልምድ ልውውጥ እንደሚደረግበት ተመላክቷል።

ኢትዮጵያ ባለፈው ዓመት ደቡብ አፍሪካ ኬፕታውን ተደርጎ በነበረው ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ነው ለአዘጋጅነት የተመረጠችው።



ኢትዮጵያ በአጭር ጊዜ ውስጥ ዲጂታል ማንነትን ለማረጋገጥ ያደረገችው ጥረትና የመንግስት ቁርጠኝነት የዘንድሮውን ጉባኤ በአዘጋጅነት እንድትመረጥ ማስቻሉም በወቅቱ ተገልጿል።

በብሄራዊ መታወቂያ ፕሮግራም የባለድርሻ አካላት ዳይሬክተር ሳሚናስ ሰይፉ ለኢዜአ እንዳሉት ኢትዮጵያ ለዲጂታል መሰረተ ልማት ግንባታ ልዩ ትኩረት ሰጥታ እየሰራች ነው።

ባለፈው ዓመት በተካሄደው ፎረም በተለይም ከስደተኞች ጋር ተያይዞ ያከናወነቻቸው ተግባራት ለበርካታ ሀገራት በተሞክሮነት ተወስዷል ብለዋል።

ነገ በይፋ በሚከፈተው አለም አቀፍ ጉባኤ ከተለያዩ የዓለም ሀገራት የተውጣጡ ተሳታፊዎች እንደሚታደሙና በዲጂታል ማንነት ዙሪያ ልምድ ልውውጥ አንደሚካሄድም ጠቁመዋል።

ባለፉት 2 ዓመታት ከ15 ሚሊዮን በላይ ዜጎች የፋይዳ መታወቂያ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጸው፤ ከ50 በላይ ተቋማት ዲጂታል መታወቂያን በሲስተማቸው አካተው አገልግሎት እየሰጡ ነው ብለዋል።

ይህም በተለይ ደህንነቱ የተረጋገጠ አገልግሎት ከመስጠት ባለፈ አገልግሎት አሰጣጡን ለማቀላጠፍና የዜጎችን እርካታ ለመጨመር እንደሚያስችል ተናግረዋል።

ኢትዮጵያ ጠንካራና ቀጣይነት ያለው ዲጂታል ማንነት ሥነ-ምህዳር ለመፍጠር የጀመረቻቸው ስራዎች ውጤት እያመጡ መሆኑንም አንስተዋል።

ፋይዳ በሲቪል ምዝገባና ነዋሪዎች አገልግሎት፣ ለፋይናንስ ዘርፉና ለሌሎች አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ምቹ መደላድል መፍጠሩንም ተናግረዋል።

ለሌሎች ሀገራት በተሞክሮነት የሚወሰድ መሆኑን ጠቅሰው ኢትዮጵያም ከሀገራት ልምድ ትቀስማለች ብለዋል።

ነገ በሚጀመረው አይዲ 4 አፍሪካ አለም አቀፍ ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባዔ የተለያዩ ሀገራት በዲጂታል ማንነት ላይ ያከናወኗቸውን ስራዎች ከማቅረብ ባለፈ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ የፓናል ውይይቶች ይካሄዳሉ ተብሎ ይጠበቃል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.