የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

የኢ-ኮሜርስ መስፋፋትን ታሳቢ ያደረገ ቀልጣፋ የሎጂስቲክስ አቅምን ለማጠናከር የግሉ ዘርፍ ሚና ወሳኝ ነው

May 26, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ግንቦት 14/2017(ኢዜአ)፦ዓለም አቀፋዊና ሀገራዊ የኢ-ኮሜርስ መስፋፋትን ታሳቢ ያደረገ ዘመናዊና ቀልጣፋ የሎጂስቲክስ አገልግሎት አቅምን ለማጠናከር የግሉ ዘርፍ ሚና ወሳኝ መሆኑን የትራንስፖርት እና ሎጀስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ ደንጌ ቦሩ ገለጹ፡፡

የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ሚኒስቴር ከኢ-ኮሜርስና የሎጂስቲክስ ዘርፍ ባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር መስራት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት አካሒዷል፡፡

የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ ደንጌ ቦሩ በዚሁ ወቅት፤ የሎጂስቲክስ ዘርፉ ለሀገር ብልጽግና መረጋገጥ የጀርባ አጥንት ነው ብለዋል፡፡

ብሔራዊ የሎጂስቲክስ ስትራቴጂ በመቅረፅ ባለፉት ዓመታት የአገልግሎት ስርዓቱን ቀልጣፋ ማድረግ የሚያስችሉ አሰራሮች ተግባራዊ እየተደረጉ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

በተለይም በዓለም አቀፍ ደረጃ የንግድ ስርዓቱ ከመደበኛ ወደ ዲጅታል ወይም ኢ-ኮሜርስ ስርዓት እየተሸጋገረ መሆኑን ጠቅሰው፥ ኢትዮጵያም በዚሁ የሽግግር ጉዞ ላይ ናት ብለዋል።

በዲጅታል የሚፈጸም የግብይት ስርዓት መስፋፋትን ታሳቢ ያደረገ የሎጂስቲክስ አቅም መገንባት ደግሞ የሸቀጦችን ዝውውር በማፋጠን ሀገራዊ ተወዳዳሪነትንና ተጠቃሚነትን ያሳድጋል ነው ያሉት።

በዲጅታል መንገድ ግብይት የተፈጸመባቸውን ሸቀጦች ከአንዱ ሀገር ወደ ሌላ ሀገር ወይም ከአንድ አካባቢ ወደሌላኛው መዳረሻ ለማዳረስ ፈጣን፣ ዝቅተኛ የማጓጓዣ ዋጋ የሚጠይቅና ዘመናዊ የሎጂስቲክስ ስርዓት መዘርጋት አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል።

በኢትዮጵያ ባለፉት የለውጥ ዓመታት በተከናወኑ ተግባራት የሀገሪቱን ገቢና ወጪ ንግድ እንዲሁም የውስጥ ግብይቶችን የሚያሳልጥ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ስርዓት እየተገነባ እንደሚገኝ አንስተዋል።

በተለይም ዲጅታል አሰራሮችን በመዘርጋት አበረታች ውጤት መምጣቱን ጠቅሰው፥ ይህን ይበልጥ አጠናክሮ ለመቀጠል የግሉ ዘርፍ ሚና ጉልህ እንደሆነም ገልጸዋል።

በተለይም የጭነት ዕቃዎችን በማጓጓዝ ስራ ላይ የተሰማሩ አካላት አገልግሎታቸውን እንዲያዘምኑና እንዲያጠናክሩ አጽንኦት ሰጥተዋል።

ኢዜአ ካነጋገራቸው የመድረኩ ተሳታፊዎች መካከል የየስ ኤክስፕሬስ ኩሪየስ አገልግሎት የአዲስ አበባ ቅርንጫፍ ዳይሬክተር ይርጋለም ደምሴ፤ ዲጅታል የግብይት ስርዓት ወይም ኢ-ኮሜርስ እና ፈጣን የሎጂስቲክስ አገልግሎትን በተናበበ መልኩ መተግበር ገንዘብ እና ጉልበትን በእጅጉ ይቆጥባል ብለዋል፡፡

መንግስት ለዘርፉ የሰጠው ትኩረት የሚደነቅ መሆኑን ጠቅሰው፤ ይህን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ ሚናችንን እንወጣለን ያሉት፡፡

የኢታ ሶሉሽን ስፔር ዋና ስራ አስኪያጅ ተመስገን ገብረ ህይወት (ዶ/ር) በበኩላቸው፤ የሎጂስቲክስ ዘርፉን ማዘመን የግብይት ስርዓትን ለማፋጠን ትልቅ አስተዋጽኦ እንዳለው ገልጸዋል፡፡

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.