የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

በዞኑ ባለፉት አስር ወራት ከ3 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ ተሰብስቧል

May 26, 2025

IDOPRESS

አምቦ፤ ግንቦት 17/2017(ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ሸዋ ዞን ባለፉት አስር ወራት ከ3 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር በላይ ገቢ መሰብሰቡን የዞኑ ገቢዎች ጽህፈት ቤት አስታውቋል።

ግብርን በዘመናዊ አሰራር እንዲከፍሉ መደረጉ ጊዜና ገንዘባቸውን እንደቆጠበላቸው የምዕራብ ሸዋ ዞን ግብር ከፋዮች ተናግረዋል።

የጽህፈት ቤቱ ኃላፊ ፍቃዱ ለማ በዞኑ ከታክስና ከተለያዩ የገቢ አርዕስቶች በበጀት ዓመቱ ለመሰብሰብ ከታቀደው 5 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ባለፉት አስር ወራት ከ3 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር በላይ መሰብሰቡን ገልጸዋል።

ገቢው በ2016 በጀት ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር በ1 ነጥብ 8 ቢሊዮን ብር ብልጫ እንዳለውም አክለዋል።

ለግብር ከፋዮች የተሰጠው የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርትና እንደ ቴሌ ብር ያሉ ቴክኖሎጂዎች ግብርን ለመክፈል ጥቅም ላይ መዋላቸው ለገቢው ማደግ ምክንያት መሆናቸውን ገልጸዋል።

በበጀት ዓመቱ የግብር አሰባሰብን ከማዘመን ባለፈ ደረሰኝ ሳይቆርጡ ሽያጭ በማከናወን ህግን በተላለፉ 67 ድርጅቶች ላይ ህጋዊ እርምጃ መወሰዱንም አመልክተዋል፡፡

ከዞኑ ግብር ከፋዮች መካከል በምግብ ዘይትና በከብቶች መኖ ማምረት ሥራ ላይ የተሰማሩት አቶ አሰግድ አለማየሁ በዲጂታል አሰራር የታገዘ የገቢ አሰባሰብ ሥርዓት መዘርጋቱ ከዚህ በፊት ግብር ለመክፈል ያባክኑት የነበረውን ጊዜና ገንዘብ እንደቆጠበላቸው ተናግረዋል።

የግብር አሰባሰብ ሂደቱ በቴክኖሎጂ የተደገፈ መሆኑ ቀደም ሲል ግብር ለመክፈል ወረፋ በመጠበቅ ሲባክንበት የነበረውን ጊዜ መቆጠቡን የገለጸው ደግሞ ሌላው ግብር ከፋይ ወጣት አበበ ሀይሉ ነው።

የዲጂታል አሰራሩ ተግባራዊ መደረጉ ግብሩን በወቅቱ በመክፈል የዜግነት ግዴታውን በአግባቡ እንዲወጣ እንዳስቻለውም ነው የተናገረው።

ግብርን በወቅቱ ለመክፈል እንቅፋት የነበሩ አሰራሮችን ለመፍታት በቴክኖሎጂ የተደገፈ የግብር አሰባሰብ ሥርዓት መጀመሩ ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት የገለጹት ደግሞ አቶ ፍቃዱ ደሳለኝ የተባሉ ግብር ከፋይ ናቸው፡፡

የተጀመረው ቀልጣፋ አሰራር የዜግነት ግዴታቸውን በአግባቡ መወጣት እንዳስቻላቸው ጠቁመው ግብር ለሁለንተናዊ የልማት እንቅስቃሴ ያለውን ፋይዳ በመረዳት ሁሉም ግብሩን በወቅቱ መክፈል እንዳለበትም ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.