የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

የኢትዮጵያ የባህር በር የማግኘት ጥያቄ አብሮ የመልማት መርህን ስለሚያጠናክር ለተግባራዊነቱ የበኩላችንን እንወጣለን - ነዋሪዎች 

May 30, 2025

IDOPRESS

ሆሳዕና፤ ግንቦት 21/2017(ኢዜአ)፦ የኢትዮጵያ የባህር በር የማግኘት ጥያቄ አብሮ የመልማት መርህን የሚያጠናክር በመሆኑ ለተግባራዊነቱ የበኩላቸውን እንደሚወጡ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል አስተያየታቸውን የሰጡ ነዋሪዎች ገለጹ፡፡

አስተያየታቸውን ለኢዜአ ከሰጡት የሀዲያና ከምባታ ዞኖች ነዋሪዎች መካከል የሆሳዕና ከተማ ነዋረሪው አበራ ሽጉጤ(ዶ/ር) እንዳሉት ሀገሪቱ የነበራትን የባህር በር ባልተገባ ምክንያት አጥታለች።

የባህር በር በሀገሪቱ እየተመዘገበ ያለውን ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ለማሳለጥና የውጭ ንግድ እንቅስቃሴንለማቀላጠፍ እንደሚረዳ ገልጸው፣ በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያን የባህር በር የማግኘት ጥያቄን ለማሳካት የዜጎች የነቃ ተሳትፎ ወሳኝ ነው ብለዋል።

የባህር በር መኖር የውጭ ኢንቨስትመንትን በማነቃቃት ለዜጎች ሁለንተናዊ ተጠቃሚነት መረጋገጥ ፋይዳው የጎላ ነው ሲሉም ገልጸዋል።

የሀገርን የባህር በር ጥያቄ ለማሳካት መንግስት ህዝብን በማሳተፍ የጀመረውን የሰከነ ፖለቲካዊና ዲፕሎማሲያዊ አካሄድ በቀጣይም አጠናክሮ መቀጠል አለበት ነው ያሉት፡፡

በተለይም የጋራ ተጠቃሚነት መርህን መሰረት በማድረግ መንግስት ያቀረባቸው አማራጮች ወሳኝ መሆናቸውን አንስተዋል።


በሀዲያ ዞን የሾኔ ከተማ ነዋሪ ወጣት በፍቃዱ ኤርሚያስ በበኩሉ የኢትዮጵያን ህዝብ ቁጥር ከግምት ያስገባ ኢኮኖሚያዊ እድገትን ለማስመዝገብ የባህር በር ጥያቄው መሰረታዊ ጉዳይ መሆኑን ተናግሯል።

የባህር በር የተጀመረውን ሀገራዊ የዕድገት ጉዞ ለማፋጠንና የዜጎችን በተለይ የወጣቱንተጠቃሚነት ስለሚያሳድግ ለውጤታማነቱ የበኩሉን እንደሚወጣ ተናግሯል፡፡


ፈጣንና ሁለንተናዊ እድገት ለማስመዝገብ የንግድ ስርዓቱን ማቀላጠፍና ተወዳዳሪነቱን ማሳደግ ያስፈልጋል ያለው ደግሞ፣ የካምባታ ዞን ዱራሜ ከተማ ነዋሪው ወጣት ሰለሞን አቡቴ ነው።

ለዚህም የባህር በር መኖር መሰረታዊ ጉዳይ መሆኑን ጠቅሶ የኢትዮጵያ የባህር በር ጥያቄ ከግብ እንዲደርስ ሁሉም ዜጋ ከመንግስት ጎን ሆኖ መስራት አለበት ብሏል።


የባህር በር የማግኘት ጥያቄው ምላሽ ማግኘት ለሀገር እድገት የሚያበረክተው ፋይዳ የጎላ መሆኑን የተናገረችው ደግሞ ሌላዋ የዱራሜ ከተማ ነዋሪ ወጣት ሌሞወርቅ ሀይለማርያም ናት።

መፍትሄ ለማምጣት መንግስት የጀመረውን አካሄድ በመደገፍ የሚጠበቅብንን እንወጣለን ብላለች፡፡

የባህር በር ማግኘት ቀጠናዊ ትስስርን የማጠናከርና የገቢና ወጪ ምርት ንግድን በማሳለጥ የዜጎችን ተጠቃሚነት የበለጠ ያሳድጋል ያለችው ወጣቷ፣ ለዚህም በመንግስት የተጀመረው ጥረት እንዲሳካ የበኩሏን ለመወጣት መዘጋጀቷን ተናግራለች።

መንግስት የሀገሪቱን የባህር በር ጥያቄ ዓለም አቀፍ መርህን በተከተለ መልኩ ምላሽ እንዲያገኝ ለማስቻል ትኩረት ሰጥቶ እየተንቀሳቀሰ መሆኑም የሚታወቅ ነው፡፡

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.