የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

በመዲናዋ የተገነቡ መሰረተ ልማቶች የተፈለገውን አገልግሎት እንዲሰጡ በአግባቡ መጠቀም እና ማስተዳደር ይገባል - ቢሮው

May 30, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ ግንቦት 21/2017(ኢዜአ)፦ በመዲናዋ የተገነቡ የትራንስፖርት መሰረተ ልማቶች የተፈለገውን አገልግሎት መስጠት እንዲችሉ በአግባቡ መጠቀም እና ማስተዳደር እንደሚገባ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የትራንስፖርት ቢሮ አስገነዘበ።

ቢሮው ”በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኮሪደር ልማት ያስገኛቸውን የትራንስፖርት መሰረተ ልማት መልካም አጋጣሚዎች በአግባቡ መጠቀምና ማስተዳደር” በሚል መሪ ሃሳብ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት አድርጓል።

የቢሮው ምክትል ኃላፊ ወርቁ ደስታ በዚሁ ጊዜ እንዳሉት፤ አስተዳደሩ መዲናዋን ስማርት ከተማ ማድረግ የሚያስችሉ የተለያዩ ተግባራት በማከናወን ላይ ይገኛል።

ከእነዚህ በርካታ የልማት ስራዎች መካከል በከተማዋ እየተገነቡ የሚገኙ የኮሪደር ልማት እና የመልሶ ግንባታ ስራዎችን ለአብነት አንስተዋል፡፡

በከተማው እየተገነቡ የሚገኙ የኮሪደር ልማት ስራዎች ውጤታማና ዘላቂ የትራንስፖርት ሥርዓት ለመዘርጋት ትልቅ ሚና እንዳላቸው አስረድተዋል።

የመሰረተ ልማት ሥራዎቹ ዘመናዊ የትራንስፖርት መሰረተ ልማትን ያሟሉና ደረጃቸውን የጠበቁ የመኪና፣ የእግረኛና የብስክሌት መንገድ፣ የመኪና ማቆሚያ ተርሚናሎችና የትራፊክ ምልክቶች ማካተታቸውን ጠቅሰዋል።

የመንገድ መሠረተ ልማቶቹ የትራንስፖርት እንቅስቃሴን በማሳለጥ ለማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴ እድገት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከቱ ነው ብለዋል።

በመሆኑም የትራንስፖርት መሰረተ ልማቶቹ የተፈለገውን አገልግሎት እንዲሰጡ በአግባቡ መጠቀም እና ማስተዳደር አስፈላጊ መሆኑን አስታውቀዋል።

ቢሮው ተገልጋዮች መሰረተ ልማቶቹን በአግባባቡ እንዲጠቀሙ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመቀናጀት የግንዛቤ ማስጨበጥ ሥራዎች ላይ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑት ቢቂላ ተክሉ(ዶ/ር) በበኩላቸው በከተማዋ በኮሪደር ልማት የተገቡ የትራንስፖርት መሰረተ ልማቶች የከተማዋን የስማርት ሲት ጉዞ የሚያሳልጡ ናቸው ብለዋል።

እነዚህን መሰረተ ልማቶች በዘላቂነት እና ደህንነታቸው በተጠበቀ መልኩ ጥቅም እንዲሰጡ ትኩረት መደረግ እንዳለበት ምክረ ሃሳብ ሰጥተዋል።

በአዲስ አበባ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑት አስራት ሙላቱ(ዶ/ር) እንደገለጹት መሰረተ ልማቶቹ ቀጣይ ትውልድን መሰረት አድርገው የተገነቡ ናቸው።

ስለዚህ ህዝቡ እነዚህን መሰረተ ልማቶች በባለቤትን መጠቀም እንዳለበት ነው ያስገነዘቡት።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.