አዲስ አበባ፤ ግንቦት 25/2017(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ኢምፖርት ኤክስፖርት (አፍሪ ኤግዚም) ባንክ በኢትዮጵያ ንግድና ኢንቨስትመንትን ለማሳለጥ የሚያደርገውን ድጋፍ የበለጠ እንዲያሳድግ አስቻይ ሁኔታዎች መፈጠራቸውን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክ አስታወቀ።
በአፍሪካ ኢምፖርት ኤክስፖርት ባንክ የተዘጋጀ በኢትዮጵያ ንግድና ኢንቨስትመንት ዕድገት ላይ ያተኮረ ውይይት በአዲስ አበባ እየተካሄደ ነው።
በውይይቱ መክፈቻ ላይ የብሄራዊ ባንክ ምክትል ገዥ ፍቃዱ ድጋፌ እንደገለጹት ባንኩ የኢትዮጵያን የቢዝነስ እንቅስቃሴዎች በመደገፍ በኩል ጉልህ ሚና እየተጫወተ ነው ብለዋል።
ባንኩ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ከ14 የግል ባንኮች ጋር እየሰራ መሆኑን ጠቅሰው፣ ይህን የበለጠ እንዲያጠናክር እንፈልጋለን ነው ያሉት።
ኢትዮጵያ ያካሄደችው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ሪፎርም ባንኩ በኢትዮጵያ ንግድና ኢንቨስትመንት ላይ የሚያደርገውን ድጋፍ የበለጠ እንዲያጠናክር አስቻይ ሁኔታ መፍጠሩን አንስተዋል።
ባንኩ በኢትዮጵያ ከውጭ ለሚገቡ ስትራቴጂክ ሸቀጦች ዋስትና በመስጠትም እያገዘ መሆኑን ተናግረዋል።
የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው የባንኮችን የውጭ ምንዛሬ እጥረት በማቃለሉ ከባንኩ ጋር በጋራ የመስራት ዕድላቸውን ማሳደጉንም ገልጸዋል።
ከዚህ አኳያ አፍሪ ኤግዚም ባንክ ለኢትዮጵያ የንግድና ኢንቨስትመንት ዘርፍ ባንኮች የተሻለ ድጋፍ እንዲያደርግ የሚያስችል መሆኑንም ነው የጠቀሱት።
የአፍሪካ ኢምፖርት ኤክስፖርት(አፍሪ ኤግዚም) ባንክ የደንበኞች ግንኙነት ተጠባባቂ ዳይሬክተር ኢሪክ ሞንቹ ባንኩ የንግድ ልውውጥን ለማሳለጥና የኢንዱስትሪ ልማትን ለማፋጠን የተለያዩ ተግባራትን እያከናወነ ነው ብለዋል።
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ፈጣን ኢኮኖሚ እያስመዘገቡ ካሉ ግንባር ቀደም ሀገራት መካከል አንዷ መሆኗን ጠቅሰው የተገበረችው የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በንግድና ኢንቨስትመንት እንዲሁም በኢንዱስትሪው ላይ ተጨባጭ ውጤት ማስመዝገቡን ገልጸዋል።
የዋጋ ግሽበትን ከመቀነስ አኳያም የተከናወኑ ስራዎች ውጤታማ መሆናቸውን ተናግረዋል።
የባንክ ሥራ አዋጁ መሻሻል ለፋይናንስ ዘርፋ ምቹ የስራ ከባቢ በመፍጠር በኩል ጉልህ ድርሻ እንዳለውም አንስተዋል።
ኢትዮጵያ ለባንክ ሥራ ምቹና አስተማማኝ መሆኗን ጠቅሰው፤ ከዘርፉ የበለጠ ተጠቃሚ እንድትሆን ባንኩ አስፈላጊውን ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል።
የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ ህሊና በላቸው፣ ባንኩ ለመሰረተ ልማት ግንባታ የሚያደርገውን ድጋፍ የበለጠ እንዲያጠናክር በጋራ መስራት የሚያስችሉ ዕድሎች መፈጠራቸውን ተናግረዋል።
የአፍሪካ ኢምፖርት ኤክስፖርት(አፍሪ ኤግዚም) ባንክ በአፍሪካ ከአፍሪካ ውጪ ንግድና ኢንቨስትመንትን ለማሳለጥ በባለብዙ ወገን ትብብር የተቋቋመ ሲሆን ኢትዮጵያም እኤአ ከ1994 ጀምሮ የባንኩ አባል ሆናለች።
ቦንጋ ፤የካቲት 16/2017 (ኢዜአ) ፡-በቦንጋ ከተማ የተካሄደውን የህዝብ ውይይት የመሩ ከፍተኛ የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች በከተማው የተለያዩ የልማት ...
Feb 24, 2025
ደብረብርሀን፤ የካቲት 15/2017(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ገበያን ለማረጋጋት የሚያግዙ ከአንድ ነጥብ አንድ ቢሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የገበያ ማዕከላት ግንባታ...
Feb 24, 2025
አዲስ አበባ፤ የካቲት 1/2017(ኢዜአ)፡- በሚቀጥሉት አምስት አመታት በወረቀት የሚካሔዱ አሰራሮችን በማስቀረት የዲጂታል ቴክኖሎጂ ግብይትና አገልግሎት በተሻለ ...
Feb 8, 2025