አዲስ አበባ፤ግንቦት 29/2017 (ኢዜአ):-የኢትዮጵያ መንግስት ደፋር የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ እርምጃዎችን በመውሰዱና ሁኔታዎችን በመቀየሩ ሀገሪቷን ወደፊት እንድትጓዝ ማስቻሉን በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ ገለፁ።
በኢትዮጵያ እና አሜሪካ መካከል ያለው ንግድ እና ኢንቨስትመንት እያደገ መምጣቱንም ገልጸዋል።
በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ኤርቪን ማሲንጋ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደገለጹት፤የኢትዮጵያ መንግስት በድፍረት የወሰዳቸው እርምጃዎች ሀገሪቷ ላይ ጠቃሚና ትርጉም ያላቸው ለውጦች አምጥቷል።
ከማሻሻያዎቹ መካከል የውጭ ምንዛሪ ተመን አንዱ መሆኑን አስታውሰው፤ይህ ማሻሻያ በመደረጉ ለበርካታ ዓመታት ያልታየ የውጭ ምንዛሪ ገበያ መረጋጋት መከሰቱን ጠቁመዋል።
የኢትዮጵያ መንግስት ቁልፍ ውሳኔዎችን በማሳለፉ የተገኙ ለውጦች መኖራቸውን ያመለከቱት አምባሳደሩ፤ በዚህም የመንግስትን ጥረት አድንቀዋል።
በኢትዮጵያ እና አሜሪካ መካከል ያለው ንግድ እና ኢንቨስትመንት እያደገ መምጣቱን የገለጹት አምባሳደር ማሲንጋ፤ በቀጣይም በሁለቱ ሀገሮች መካከል ያለውን የንግድ ግንኙነት ለማስፋፋት ፍላጎት መኖሩን ተናግረዋል።
ኢትዮጵያ ሰፊ የወጪ ንግድ አቅም እንዳላት ያብራሩት አምባሳደሩ፤ በተለይም የቡና፣ ሻይ፣ ጤፍ፣ አበባ እና የማዕድን ሀብቶችን ወደ አሜሪካ በመላክ የውጭ ምንዛሬ የማግኘት አቅም እንዳላት ጠቁመዋል፡፡
ቀደም ሲል ኢትዮጵያ የግሉ ዘርፍ ተሳትፎ የሚገድብ የኢኮኖሚ ማዕቀፍ ውስጥ ስትንቀሳቀስ መቆየቷን አውስተው፤አሁን ያለው መንግስት የግሉን ዘርፍ ተሳትፎ ለማሳደግ የወሰደው የፖሊሲ እርምጃንም አድንቀዋል።
በአሁኑ ወቅት ቡናን ጨምሮ ወደ አሜሪካ የሚላኩ ምርቶችን ለማስፋት ትልቅ ዕድል መኖሩን ጠቁመው፤እነዚህን ዕድሎች ለማስፋትም ከኢትዮጵያ መንግስት እና የንግድ ማህበረሰብ ጋር በጋራ እንደሚሰሩም አረጋግጠዋል፡፡
በኢትዮጵያና በአሜሪካ መካከል ያለው ዘላቂ ትብብር ያደነቁት አምባሳደር ማሲንጋ፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የቆየ አጋርነት የሚያጎላ ነው ሲሉ ጠቅሰዋል።
በተጨማሪም አሜሪካ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በቢሾፍቱ የሚገነባውን አውሮፕላን ማረፊያ በማልማት ረገድ ዕድሎች ለማየት በንቃት ለመሳተፍ ፍላጎት እንዳላት አመላክተዋል።
ቦንጋ ፤የካቲት 16/2017 (ኢዜአ) ፡-በቦንጋ ከተማ የተካሄደውን የህዝብ ውይይት የመሩ ከፍተኛ የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች በከተማው የተለያዩ የልማት ...
Feb 24, 2025
ደብረብርሀን፤ የካቲት 15/2017(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ገበያን ለማረጋጋት የሚያግዙ ከአንድ ነጥብ አንድ ቢሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የገበያ ማዕከላት ግንባታ...
Feb 24, 2025
አዲስ አበባ፤ የካቲት 1/2017(ኢዜአ)፡- በሚቀጥሉት አምስት አመታት በወረቀት የሚካሔዱ አሰራሮችን በማስቀረት የዲጂታል ቴክኖሎጂ ግብይትና አገልግሎት በተሻለ ...
Feb 8, 2025