ባህርዳር፤ ሰኔ 3/2017 (ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል አገልግሎት አሰጣጡን በማዘመን የተገልጋዩን ጊዜና ጉልበት በመቆጠብ ፍትሃዊ አገልግሎት እንዲያገኝ ጥረት እየተደረገ መሆኑ ተመላከተ።
የባህር ዳር ከተማ በመንግስት አገልግሎትና ስታንዳርድ ሪፎርም አተገባበር ላይ የንቅናቄ መድረክ ዛሬ አካሄዷል።
በንቅናቄ መድረኩ የመወያያ ጽሁፍ ያቀረቡት በክልሉ ሲቪል ሰርቪስና የሰው ሃብት ልማት ኮሚሽን የሪፎርም ድጋፍና ክትትል ዳይሬክተር አቶ እንዳለው ይታይ እንደገለጹት በአገልግሎት አሰጣጥ ረገድ ሰፊ ቅሬታ የሚያስነሳው ቀልጣፋና ፍትሃዊ አገልግሎትን ለህብረተሰቡ ተደራሽ አለማድረግ ነው።
ችግሩን ለመቅረፍ እንደ ሀገር የወጣውን ፖሊሲ መሰረት በማድረግ አገልግሎት አሰጣጡን ዲጂታላይዝ በማድረግ ተገልጋዩ ጊዜና ጉልበቱን ከመቆጠብ በተጨማሪ ፍትሃዊነቱ የተረጋገጠ አገልግሎት እንዲያገኝ ስራዎች እየተሰሩ ነው ብለዋል።
ለመልካም አስተዳደር ችግሮችና ብልሹ አሰራሮች ምክንያት ከሆኑት አንዱ የሆነው ሀሰተኛ የትምህርት ማስረጃን የመለየት ስራ እየተከናወነ እንደሚገኝም ገልጸዋል።
በዚህም እስከ ሰኔ 2017 ዓ.ም መጨረሻ ባለው ጊዜ የትምህርት ማስረጃ ለይቶ ለማጠናቀቅ ታስቦ እየተሰራ መሆኑንም ጠቁመዋል።
የአገልግሎት አሰጣጡ እውቀትንና ክህሎትን መሰረት ባደረገ አግባብ እንዲመራ ሲቪል ሰርቫንቱ እንደየ ዘርፉ የረጅም ጊዜና የስራ ላይ ስልጠና እንዲያገኝ የሚያስችሉ ተግባራትም እየተከናወኑ እንደሚገኙ ተናግረዋል።
የዘመነና የባህር ዳር ከተማን የሚመጥን የመንግስት አገልግሎትን ተደራሽ ለማድረግ የዲጂታል አገልግሎት አሰጣጥን መተግበር ቀዳሚ ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ መሆኑን የገለጹት ደግሞ የከተማዋ ምክትል ከንቲባ አቶ አስሜ ብርሌ ናቸው።
ከተማ አስተዳደሩ ከሚሰጠው ሰፊ አገልግሎት አንጻር የተቀላጠፈ አገልግሎት በመስጠት በኩል የሚነሱ ቅሬታዎችን መፍታት የሚቻለው በቴክኖሎጂ የታገዘ አገልግሎትን ተደራሽ ማድረግ ሲቻል መሆኑን አንስተው ይህንን ታሳቢ ያደረጉ ተግባራት በመከናወን ላይ መሆናቸውን ገልጸዋል።
በንቅናቄ መድረኩ ላይ የተገኙት የአማራ ክልል መሬት ቢሮ ኃላፊ አቶ ሲሳይ ዳምጤ እንደገለጹት የመንግስት አገልግሎትና ስታንዳርድ ሪፎርም ውጤታማ የሚሆነው በየደረጃው ያለ አመራር ኃላፊነቱን በአግባቡ መወጣት ሲችል ነው።
የንቅናቄ መድረኩ አላማም በየደረጃው ያለ አመራር ስለ ሪፎርሙ በአግባቡ ተገንዝቦ ለተግባራዊነቱ እንዲተጋ ማስቻል ነው ብለዋል።
በአማራ ክልል ከግማሽ ሚሊዮን በላይ የሚሆን ሲቪል ሰርቫንት እንዳለም መረጃዎች ያመላክታሉ።
ቦንጋ ፤የካቲት 16/2017 (ኢዜአ) ፡-በቦንጋ ከተማ የተካሄደውን የህዝብ ውይይት የመሩ ከፍተኛ የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች በከተማው የተለያዩ የልማት ...
Feb 24, 2025
ደብረብርሀን፤ የካቲት 15/2017(ኢዜአ)፡- በአማራ ክልል ገበያን ለማረጋጋት የሚያግዙ ከአንድ ነጥብ አንድ ቢሊዮን ብር በሚበልጥ ወጪ የገበያ ማዕከላት ግንባታ...
Feb 24, 2025
አዲስ አበባ፤ የካቲት 1/2017(ኢዜአ)፡- በሚቀጥሉት አምስት አመታት በወረቀት የሚካሔዱ አሰራሮችን በማስቀረት የዲጂታል ቴክኖሎጂ ግብይትና አገልግሎት በተሻለ ...
Feb 8, 2025