የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

በክልሉ ቡናን በመጉንደል እና በንቅለ ተከላ በማሻሻል ምርታማነት እያደገ ነው

Jun 23, 2025

IDOPRESS

ክልል፤ሰኔ 14/2017 (ኢዜአ)- በኦሮሚያ ክልል ቡናን በመጉንደልና በንቅለ ተከላ ስራ በማሻሻል የዘርፉ ምርትና ምርታማነት እያደገ መምጣቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ።

የክልሉ ግብርና ቢሮ ምክትልና የቡናና ሻይ ዘርፍ ሃላፊ አቶ መሐመድ ሳኒ አሚን፤ በእርጅና እና በሽታ ምክንያት የቡና ምርታማነት ሊቀንስ እንደሚችል በተግባር መታየቱን ገልጸዋል።


ይህንን በመለወጥ የዘርፉን ምርታማነት ይበልጥ ለማሳደግ ከ2011ዓ.ም ጀምሮ በክልሉ በከፍተኛ ንቅናቄ በእርጅና ምክንያት ምርት የማይሰጡትን በመጉንደል፤ በበሽታ የተጠቁና በደረቁት ቦታዎች የንቅለ ተከላ ስራ ርብርብ ሲደረግ መቆየቱን ተናግረዋል።

በዚህም የቡና ምርትና ምርታማነት ይበልጥ እያደገ እንዲመጣ ማስቻሉን ገልጸዋል።

ከ2011ዓ.ም ጀምሮ እስካሁን በተደረገው ርብርብ በክልሉ በጉንደላና በንቅለ ተከላ ስራ 600ሺህ ሄክታር መሬት መሸፈን መቻሉን አስታውቀዋል።

ቢሮው የቡና ልማቱን ለማሳደግ ለአርሶ አደሩ የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን ከማቅረብ ባለፈ በዘመናዊ መንገድ የሚያለሙበትን ግንዛቤ ማሳደጉን ጠቁመዋል።


ይህም ቀደም ሲል የቡና ምርት በሄክታር በአማካኝ ስድስት ኩንታል ይገኝ የነበረውን አሁን ላይ ወደ ስምንት ኩንታል ማሳደግ መቻሉን አመላክተዋል።

እንዲሁም በ2011ዓ.ም የተሰበሰበው የቡና ምርት ከአንድ ሚሊዮን ኩንታል እንደማይበልጥ አውስተው፤ ዘንድሮ ወደ 15 ነጥብ 7 ሚሊዮን ኩንታል ማደጉን ገልጸዋል።


በቀጣይም የዘርፉን ምርታማነት ይበልጥ ለማሳደግ የተሻሻሉ የቡና ዝርያዎችን በማቅረብ አርሶ አደሩን ለማገዝ እንደሚሰራ ተናግረዋል።


በኦሮሚያ ክልል በቡና ልማት የተሸፈነ ሶስት ነጥብ አንድ ሚሊዮን ሄክታር መሬት እንደሚገኝ አቶ መሐመድ አመልክተዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.