የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ዘመኑን የዋጀና ተወዳዳሪ የሚያደርገንን የዲጂታል እውቀት እና ክህሎት ጨብጠናል - ሰልጣኞች

Jul 1, 2025

IDOPRESS

ጎንደር፤ ሰኔ 20/2017(ኢዜአ)፦ በኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ዘመኑን የዋጀና ተወዳዳሪ የሚያደርጋቸውን የዲጂታል እውቀትና ክህሎት መጨበጣቸውን ስልጠናውን የተከታተሉ የጎንደር ከተማ ሰልጣኞች ተናገሩ።

የከተማ አስተዳደሩ ስራና ስልጠና መምሪያ በ2017 በጀት ዓመት የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና ተከታትለው ላጠናቀቁ የእውቅና መርሐ ግብር ዛሬ አካሂዷል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ዜጎች በዌብ ፕሮግራሚንግ፣ በአንድሮይድ ማበልፀግ፣ ዳታ ሳይንስና አርቲፊሻል ኢንተለጀንስ መሰረታዊ የዲጂታል ክህሎት እንዲኖራቸው የአምስት ሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ከደርስ ስልጠና ሐምሌ 2016 ዓ.ም ማስጀመራቸው ይታወሳል።

በዚህም በርካታ ወጣቶች አቅማቸውን ለማሳደግ፣ ተጨማሪ የሥራ ዕድል ለመፍጠርና ዘመኑን የዋጀ የዲጂታል ቴክኖሎጂ ተጠቃሚ ለመሆን በኦንላይን ስልጠና የመከታተል ዕድል አግኝተዋል።

ስልጠናውን ካጠናቀቁት ሰልጣኞች መካከል አቶ ሽፈራው አያሌው፤ መንግስት ያመቻቸው አለም አቀፍ የስልጠና እድል ሀገሪቱ ለጀመረችው ዲጂታል መር የልማት ግንባታ ወሳኝ ነው ብለዋል።

ስልጠናው ዘመኑን የዋጀና አለም አቀፍ ብቃትን በማረጋገጥ ተወዳዳሪነትን የሚያላብስ መሆኑንም ተናግረዋል።

ሌላዋ የዕድሉ ተጠቃሚ ወጣት የሻረግ ልጃለም በበኩሏ፤ ስልጠናው በአስተሳሰብ፣ በፈጠራና በቴክኖሎጂ አጠቃቀም የነበረብኝን ክፍተት መሙላት አስችሎኛል ብላለች።

ከዘመኑ የቴክኖሎጂ እድገት ጋር አብሮ የማይራመድ ትውልድና ሀገር በአለም አቀፍ ተወዳድሮ ማሸነፍ እንደማይችል ጠቁማ፤ በእድሉ በመጠቀም እውቀትና ክህሎቷን ማሳደጓ እንዳስደሰታት ተናግራለች።

ወጣት በቃሉ ገነቱ፤ ትውልድን ዘመኑ ባፈራው የዲጂታል ቴክኖሎጂ ለማነጽ እራስን አስቀድሞ ማብቃት እንደሚገባ በማመን መሰልጠኑን ተናግሯል።

አሁን ላይ ስልጠናውን አጠናቆ ማረጋገጫ ሰርተፊኬት ማግኘቱን ጠቅሶ፤ ባገኘሁት እውቀትና ክህሎት ሀገሬ ለጀመረችው የዲጂታል ቴክኖሎጂ ሪፎርም ስኬታማነት የድርሻዬን ለማበርከት ዝግጁ ነኝ ብሏል።

በበጀት ዓመቱ በከተማ አስተዳደሩ ከ10 ሺህ በላይ ወጣቶች የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና መጀመራቸውን የገለጹት የከተማው ስራና ስልጠና መምሪያ ሃላፊ ላቂያው አንዳርጌ ናቸው።

ስልጠናውን አጠናቀው ዛሬ ሰርቲፊኬት ለተቀበሉ 4ሺህ 227 ሰልጣኞች ከተማ አስተዳደሩ የእውቅና አሰጣጥ መርሀ ግብር ማካሄዱን ተናግረዋል።

ቀሪዎቹ በሂደት ላይ እንደሚገኙ ጠቅሰው፤ የኢትዮ ኮደርስ ስልጠና አለም አቀፍ ተወዳዳሪ ዜጋን በማፍራት ከሀገር ውስጥ ባለፈ በውጭ ጭምር ሰፊ የስራ ዕድል የሚያገኙበት ነው ብለዋል።

ከተማ አስተዳደሩ በ2018 በጀት ዓመት ተጨማሪ ወጣቶችን የስልጠናው ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ ከወዲሁ ዝግጅት መጀመሩን ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.