የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ፕሮሞሽን ስትራቴጂ ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻነቷን የሚያጠናክር ነው

Jul 1, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ሰኔ 23/2017(ኢዜአ)፦የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ፕሮሞሽን ስትራቴጂ ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻነቷን የሚያጠናክር መሆኑን የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘለቀ ተመስገን (ዶ/ር) ገለጹ።

ለአምስት ዓመታት የሚተገበረው ይህ ስትራቴጂ ከሐምሌ1/2017 ዓ.ም ጀምሮ ወደ ሥራ እንደሚገባም ገልጸዋል።

በስትራቴጂው ዙሪያ የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ያዘጋጀው የምክክር መድረክ ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ የተለያዩ ሀገራት አምባሳደሮች፣ የልማት አጋሮችና የግሉ ዘርፍ በተሳተፉበት ተካሂዷል።


ኮሚሽነር ዘለቀ ተመስገን(ዶ/ር) እንደገለጹት፤ ኢትዮጵያን ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻ ለማድረግ የሕግና ፖሊሲ ማሻሻያዎችን ጨምሮ በርካታ የለውጥ ተግባራት ተከናውነዋል።

ለውጭ ባለሃብቶች ዝግ የነበሩ የኢኮኖሚ መስኮች ከለውጡ ወዲህ ለኢንቨስትመንት ክፍት መደረጋቸውን ጠቅሰው፤ እነዚህን ለውጦች ውጤታማ ማድረግ የሚያስችል የኢንቨስትመንት መሳቢያ ስትራቴጂ አስፈላጊ መሆኑን አንስተዋል።

በአዲስ መልክ የተዘጋጀውና የኢትዮጵያን እምቅ የኢንቨስትመንት አቅም ለማስተዋወቅ የሚረዳው የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ፕሮሞሽን ስትራቴጂ አዳዲስ የተከፈቱ የኢንቨስትመንት መስኮችን አካትቶ መዘጋጀቱን አብራርተዋል።

ስትራቴጂው የኢትዮጵያን የኢንቨስትመንት አቅም በማስተዋወቅ ሂደት ባለድርሻ አካላት ተቀናጅተው እንዲሰሩ ከማስቻሉም በላይ ለባለሃብቶች ወጥ የሆነ የኢንቨስትመንት መረጃ ተደራሽ ለማድረግ እንደሚያግዝ አስረድተዋል።

ስትራቴጂውን ሙሉ በሙሉ ተግባራዊ ለማድረግ የድርጊት መርሃ ግብር እንደሚዘጋጅ የገለጹት ኮሚሽነሩ፤ ከሐምሌ 1 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ ወደ ሥራ ይገባል ብለዋል።

ኢትዮጵያን በአፍሪካም በዓለምም ተመራጭ የኢንቨስትመንት መዳረሻ ለማድረግ የተያዘው ሀገራዊ ግብ እንዲሳካ ስትራቴጂው ጉልህ ሚና እንደሚጫወትም ጠቁመዋል።


የቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ ስለሺ ግርማ በበኩላቸው፤ ለውጡን ተከትሎ የተሻሻለው አዲሱ የኢንቨስትመንት አዋጅ የቱሪዝም ልማትን የሚያሳልጡ አሰራሮች መያዙን ጠቅሰዋል።

በቱሪዝም ዘርፍ ለኢንቨስትመንት የሚሆኑ አካባቢዎችን የመለየት ሥራ መከናወኑን የገለጹት ሚኒስትር ደኤታው፤ በመስኩ የውጭ ኢንቨስትመንት ለመሳብ የስትራቴጂው እውን መሆን ወቅታዊ እና ትልቅ ውጤት የሚያመጣ ነው ብለዋል።

ከምክክር መድረኩ ተሳታፊዎች መካከል የሞሃን ፒ ኤል ሲ ሥራ አስኪያጅ ሀርሽ ኩታሪ እንዳሉት፤ ስትራቴጂው የውጭ ባለሃብቶችን ተሳትፎ የሚያሳድግ በመሆኑ ትልቅ እርምጃ ነው።


አንድ ኢንቨስትመንት ከመነሻው ጀምሮ አጠቃላይ ሂደቱን በቴክኖሎጂ በታገዘ መልኩ መከታተል የሚያስችል አሰራር በስትራቴጂው መካተቱም የኢንቨስትመንት ውጤታማነትን በእጅጉ የሚያሳድግ ነው ብለዋል።

የዞስካለስ ፓርትነርስ ኩባንያ ተወካይ እሴት ልዑልሰገድ በበኩላቸው፤ ኢንቨስትመንት የመሳብ ጥረት ይበልጥ ውጤታማ እንዲሆን አገልግሎት አሰጣጡን የበለጠ ለማሻሻል መሥራት ይገባል ነው ያሉት።


ለግሉ ዘርፍ ምቹ ሁኔታ ለመፍጠር የተከናወኑ ተግባራትን በተሻለ መልኩ ማስተዋወቅ እንደሚገባም አጽንኦት ሰጥተዋል።

የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ፕሮሞሽን ስትራቴጂ እ.ኤ.አ. ከ2025 እስከ 2030 ድረስ የሚተገበር ሲሆን፥ የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንትን በተሻለ መልኩ ለመሳብ የሚያስችል መሆኑም ተመላክቷል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.