የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

በቦረና ዞን እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎች የአርሶና አርብቶ አደሩን ህይወት በተጨባጭ በመቀየር ላይ ይገኛሉ

Jul 3, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ሰኔ 25/2017(ኢዜአ):-በቦረና ዞን እየተከናወኑ የሚገኙ የተለያዩ የልማት ስራዎች የአርሶና አርብቶ አደሩን ህይወት በተጨባጭ በመቀየር ላይ መሆናቸውን በብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ከፍያለው ተፈራ ገለጹ።

የኦሮሚያ ክልል ፕሬዚዳንት ሽመልስ አብዲሳ እና የክልሉ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች በቦረና ዞን እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎችን ጎብኝተዋል።


በጉብኝቱም በክላስተር እየለማ የሚገኝ የስንዴ ክላስተር፣ የቀበሌ አስተዳደር የስራ እንቅስቃሴ፣ የቦረና ከብቶች ማድለቢያ ቦታን ጨምሮ በግንባታ ላይ የሚገኘውን የቦረና ባህል ማዕከልን ጎብኝተዋል።

በብልጽግና ፓርቲ የኦሮሚያ ክልል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ኃላፊ ከፍያለው ተፈራ ጉብኝቱን አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ፤ በቦረና ዞን እየተከናወኑ የሚገኙ የልማት ስራዎች የህብረተሰቡን ህይወት በተጨባጭ እየቀየሩ ይገኛሉ ብለዋል።

በክላስተር እየለማ የሚገኘው የስንዴ ምርትም አካባቢው ላይ የስንዴ ምርታማነት እያደገ ለመሆኑ ማሣያ ነው ብለዋል።

ዞኑ ከዚህ ቀደም ተከሰቶ ከነበረው ድርቅ በማገገም ምርታማነትን በተጨባጭ እያረጋገጠ እንደሚገኝም ጠቁመዋል።

በኦሮሚያ ክልል በቅርቡ ተግባራዊ የተደረገው የቀበሌ አስተዳደር መዋቅር ህዝቡ በቅርበት አገልግሎት እንዲያገኝ ማስቻሉን ተናግረዋል።

በቦረና ዞን ደረጃቸውን የጠበቁ የቀበሌ አስተዳደር ጽህፈት ቤቶች ወደ ስራ የገቡ ሲሆን፥ የአርብቶ አደሩን እንግልት በመቀነስ የመልካም አስተዳደር ችግሮች በፍጥነት እንዲቀረፉ ማስቻሉን ጠቁመዋል።


የቦረና ዞን ዋና አስተዳዳሪ አብዱልሰላም ዋሪዮ በበኩላቸው፥ በዞኑ ከሁለት ወራት በፊት በተጀመረው የክረምት ወራት የግብርና ልማት 135 ሺህ ሄክታር መሬት በተለያዩ የዘር ዓይነቶች መሸፈኑን ገልጸዋል።

ከዚህ ውስጥም ከ56 ሺህ ሄክታር በላይ መሬት በክላስተር እየለማ መሆኑን ጠቅሰው፥ 5 ሺህ ሄክታር በስንዴ ምርት የተሸፈነ መሆኑን ጠቁመዋል።

ስንዴ፣ ቦሎቄ፣ ጤፍ፣ ማሾ እና ሌሎችም ሰብሎችን ማልማት መቻሉን በመግለፅ፥ ከዚህም 1 ነጥብ 9 ሚሊዮን ኩንታል ምርት እንደሚጠበቅ ተናግረዋል።

የቦረና ዞን አሁን ላይ በተሻለ ምርታማነት ላይ እንደሚገኝ አስረድተው፥ የአርብቶ አደሩ የስራ ባህል እየተቀየረ መሆኑን ጠቁመዋል።


በቦረና ዞን የድሬ ወረዳ ነዋሪ የሆኑት ጃተኒ ቦሩ እና አብዱላሂ ቆዳ ስንዴን በክላስተር በማልማት ምርታማ በመሆን ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል።

በመንግሥት በኩል ምርጥ ዘርን ጨምሮ የተለያዩ ግብዓት እየቀረበላቸው በመሆኑ ምርታማነትን እያሳደገልን ነው ብለዋል።

በዱቡሉቅ ወረዳ አኖሌ ቀበሌ ነዋሪዎች ኖሌ ኮርማ እና ሮባ ጎዳና የቀበሌ አስተዳደር ከመኖሪያቸው በአቅራቢያ መቋቋሙ እንግልትን እንዳስቀረላቸው ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.