የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን  ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ  የህዝብን የልማት ተጠቃሚነት የማረጋገጥ ስራ ይጠናከራል 

Oct 11, 2025

IDOPRESS

🔇Unmute

ማያ ፤ መስከረም 30/2018 (ኢዜአ)፡-በኦሮሚያ ክልል የማያ ከተማ መስተዳደር ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ አሟጦ በመሰብሰብ የህዝብን የልማት ተጠቃሚነት የማረጋገጥ ስራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታወቀ።

የከተማው መስተዳድር ገቢዎች ጽህፈት ቤት ሃላፊ አቶ አብዲ ዩያ ለኢዜአ እንደገለጹት ፤ በከተማ መስተዳድሩ ኢኮኖሚው የሚያመነጨውን ገቢ ለመሰብሰብ በሚከናወነው ስራ በየዓመቱ የሚሰበሰበው ገቢ እየጨመረ ነው።

በዚሁ ልክ በሶስቱም ክፍለ ከተሞች ለህዝብ የልማት ጥያቄዎች ምላሽ እየተሰጠ ይገኛል ብለዋል።

በዘንድሮ በጀት ዓመትም ቀጥታና ቀጥታ ካልሆኑ ታክሶች እንዲሁም ከማዘጋጃ ቤታዊ አገልግሎት ከ2 ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር በላይ ለመሰብሰብ ታቅዶ በመጀመሪያዎቹ ሶስት ወራት ከ658 ሚሊዮን ብር በላይ መሰብሰቡን ጠቅሰዋል።

የገቢ አሰባሰቡ እቅዱን ሙሉ ለሙሉ ማሳካት በሚቻል መልኩ መከናወኑን የጠቀሱት ሃላፊው ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ደግሞ በ271 ሚሊየን ብር ብልጫ ማሳየቱን አመላክተዋል።

ለገቢው መጨመር የተቀመጡትን የገቢ ርዕሶች በአግባቡ ለመተግበር የተካሄደው የተቀናጀ ጥረትና የግብር ከፋዩ ህብረተሰብ ግብርን የመክፈል ግንዛቤ እያደገ መምጣት ተጠቃሽ መሆናቸውን አቶ አብዲ አስረድተዋል።

የክልሉ መንግስት ባስቀመጠው አቅጣጫ መሰረት በራስ ገቢ ወጪን ለመሸፈን የተጀመረውን ጥረት ለማሳካት ጥረቱ ተጠናክሮ ቀጥሏል ብለዋል።

የግብር ገቢው በየዓመቱ መጨመር የህዝብ የልማት ተጠቃሚነት እንዲጎለብት እያስቻለ እንደሚገኝ ተናግረዋል።

በከተማ መስተዳድሩ የሚሰበሰበው ገቢ ላይ ተጽዕኖ የሚያስከትለውን የኮንትሮባንድ ንግድ በመከላከል ረገድ የሚከናወነው የተቀናጀ ስራ ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።

ህገ ወጥ ነጋዴዎችን ወደ ህጋዊ መስመር የማስገባትና ደረሰኝ በማይቆርጡ የንግድ ድርጅቶች ላይም የሚከናወነው የቁጥጥርና ክትትል ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አስታውቀዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.