🔇Unmute
ባሕር ዳር ፤ ህዳር 3/2018(ኢዜአ)፦የጣናነሽ ቁጥር - ሁለት ጀልባ ሥራ መጀመር በጣና ሐይቅ ሲሰጥ የቆየውን የትራንስፖርት አገልግሎት ይበልጥ በማዘመን የቱሪዝም ዘርፉን እያነቃቃ መምጣቱን በባሕር ዳር ከተማ አስጎብኚዎች ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ባለፈው ሳምንት በባሕር ዳር ከተማ ተገኝተው ጣናነሽ ቁጥር-2 ጀልባን ሥራ በይፋ ማስጀመራቸው የሚታወስ ነው።
የጀልባዋን ሥራ መጀመር በማስመልከት ኢዜአ ያነጋገራቸው የባሕር ዳር ከተማ አስጎብኚዎች እንዳሉት፤ የጀልባዋ ወደሥራ መግባት በጣና ሐይቅ ላይ የነበረን ዘመኑን የማይመጥን የትራንስፖርት አገልግሎት ቀይሮታል።
አገልግሎቱን በማዘመን ዘርፉን እያነቃቃው መምጣቱንም ነው የተናገሩት።

ከአስጎብኚዎቹ መካከል አቶ አበበ ያረጋል፤ የጀልባዋን ሥራ መጀመር በተለይ በቱሪዝም ዘርፍ የተሰማራው ማህበረሰብ በጉጉት ሲጠብቀው እንደቆየ ተናግረዋል።
ለቱሪስቶች በጣና ሐይቅ ላይ የሚገኙ ታሪካዊና ባሕላዊ የመስህብ ሃብቶችን ለመጎብኘት ትልቅ ዕድል ይዞ መምጣቱንም ተናግረዋል።
ከዚህ ቀደም በጣና ሐይቅ ዘመኑን በማይዋጅ፣ ምቾትና ፍጥነት በሌላቸው አነስተኛና ያረጁ ጀልባዎች የትራንስፖርት አገልግሎት ሲሰጥ መቆየቱን አስታውሰዋል።
አዲሷ ጀልባ ፈጣን፣ ዘመናዊና ምቾት ያላት በመሆኗ በርካታ ጎብኚዎች ጀልባዋን ለመጠቀም ጥያቄ እያቀረቡ መሆናቸውን ጠቁመዋል።
ሌላው በአስጎብኚነት ሥራ የተሰማሩት አቶ አበባው ሲሳይ በበኩላቸው፤ ከዚህ ቀደም በርካታ ጎብኚዎች በአንድ ጊዜ ሲመጡ ለማስተናገድ ይቸገሩ እንደነበር አስታውሰዋል።
የነበሩ ጀልባዎች አነስተኛና ውስን ሰው ብቻ እንደሚይዙ ጠቁመው፤ ጣናነሽ ቁጥር-ሁለት ጀልባ ብዛት ያለው ሰው የመያዝ አቅም ስላላት ችግሩ መፈታቱን ተናግረዋል።

ጀልባዋ ለጉዞ የሚያስፈልጉ ግብአቶች የተሟላላት በመሆኑ የጎብኚዎችን ቀልብ የመሳብ አቅሟም ከፍተኛ ነው ብለዋል።
አቶ ኤፍሬም አብርሀም የተባሉ ሌላው አስጎብኚ፤ የጀልባዋ ስራ መጀመር በጣና ሐይቅ ለሚከናወነው የቱሪዝም ሥራ አዲስ መነቃቃት እየፈጠረ መምጣቱን ተናግረዋል።
ሐይቁ የታሪካዊ፣ ሃይማኖታዊና ባህላዊ መስህብ ሃብት መገኛ በመሆኑ ይህን ዘርፍ ለኢኮኖሚያዊ ጥቅም ለማዋል የጀልባዋ ሥራ መጀመር ፋይዳው የጎላ ነው ብለዋል።
ከጅቡቲ ወደ ኢትዮጵያ አፋር ክልልና አዲስ አበባ አድርጋ ጠመዝማዛና አስቸጋሪውን የዓባይ በረሃን መንገድ በማቋረጥ ባሕር ዳር ከተማ የደረሰችው ጣናነሽ ቁጥር- ሁለት ጀልባ በኢትዮጵያ ባህር ትራንስፖርት እና ሎጀስቲክ አገልግሎት ድርጅት የተገዛች ናት።
ቀደም ሲል አገልግሎት ሲሰጡ ከቆዩት ጀልባዎች በዘመናዊነቷ ፣ በተገጠመላት ቴክኖሎጂ ፣ በፍጥነቷና ለጎብኚዎች ባላት ምቾት ለየት ያለች እንደሆነ ተመላክቷል።
ሆሳዕና ፤ ነሐሴ 21/2018 (ኢዜአ) ፦ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች የህዝብ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ የሚጠበቅባቸውን ሚና እንዲወጡ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ...
Aug 28, 2026
መቱ፤ ነሐሴ 11/2018 (ኢዜአ)፦ በኦሮሚያ ክልል በኢሉባቦር ዞን በክረምት እርሻ እየለማ ከሚገኘው የበቆሎ ሰብል የላቀ ምርት ለማገኘት የሰብል እንክብካቤና ጥ...
Aug 18, 2026
ሀዋሳ፤ ነሐሴ 2/2018 (ኢዜአ)፦ በሲዳማ ክልል የመንገድና ሌሎች መሰረተ ልማትን በማሻሻል ለሕዝቡ ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ መሆና...
Aug 10, 2026
አዳማ፤ ሐምሌ 12/2018 (ኢዜአ)፦በኦሮሚያ ክልል በበጀት ዓመቱ ሰላምና መልካም አስተዳደርን ከማረጋገጥ ጎን ለጎን ውጤታማ የልማት ሥራዎች መከናወናቸውን የክል...
Jul 20, 2026