የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ

በዞኑ ባለፉት አራት ወራት ከ1 ነጥብ 6 ሚሊየን ኪሎ ግራም በላይ የማር ምርት ተመርቷል

Nov 20, 2025

IDOPRESS

🔇Unmute

ደብረ ማርቆስ ፤ሕዳር 10/2018 (ኢዜአ)፡- በምስራቅ ጎጃም ዞን በበጀት ዓመቱ አራት ወራት ከ1 ነጥብ 6 ሚሊየን ኪሎ ግራም በላይ የማር ምርት ማምረት መቻሉን የዞኑ እንስሳትና አሳ ሃብት መምሪያ ገለጸ።

በአማራ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች የሌማት ትሩፋት እና ሌሎችም ኢንሸቲቮች ተግባራዊ እየተደረጉ ውጤትም እየተመዘገበባቸው ይገኛል።

የምስራቅ ጎጃም ዞን እንስሳትና አሳ ሃብት መምሪያ የንብና ሃር ልማት ባለሙያ አቶ ስማቸው ዳምጤ ለኢዜአ እንደገለጹት፤በዞኑ ከሰብል ልማት ጎን ለጎን የአካባቢውን ምቹነት በመጠቀም የንብ ማነብ ስራ በብዛትና በስፋት እየተከናወነ እና ውጤትም እየተገኘ ነው፡፡

በዚህም መሰረት በተያዘው በጀት ዓመት ከሁለት ነጥብ አንድ ሚሊየን ኪሎ ግራም በላይ የማር ምርት ለማምረት ታቅዶ እስካሁን ከ1 ነጥብ 6 ሚሊየን ኪሎ ግራም በላይ ማምረት መቻሉን ገልጸዋል።

በዘርፉ ልማት አሁን ላይ ከ11 ሺህ በላይ አርሶ አደሮች በተደራጀ መልኩ እየሰሩ መሆኑን አንስተው በዚህም ተጠቃሚ መሆናቸውን ተናግረዋል።


ከአንድ ዘመናዊ ቀፎ በአማካይ 30 ኪሎ ግራም፣ ከሽግግር ቀፎ 18 ኪሎ ግራም ከባህላዊ ቀፎ ደግሞ 8 ኪሎ ግራም የማር ምርት እየተገኘ መሆኑን ገልጸዋል።

በዞኑ አዋበል ወረዳ አነቢ ቀበሌ ነዋሪ አርሶ አደር የሻንበል እውነቱ እና በጎዛምን ወረዳ የአጭራ ቀበሌ ነዋሪ ወይዘሮ ነጠሩ አዘነ፤ በዘርፉ ልማት ተጠቃሚ ስለመሆናቸው ተናግረዋል።

በአረንጓዴ ልማት የተራቆቱ አካባቢዎች በመልማታቸው እንዲሁም ዘመናዊ የንብ ማነብ አሰራር ተግባራዊ ማድረጋቸው በዘርፉ ልማት ስኬታማ ስለመሆናቸው አንስተዋል።

በመሆኑም ሌሎች አርሶ አደሮችም ከግብርና ስራቸው በተጓዳኝ በንብ ማነብ ስራ ቢሰማሩ አትራፊ እና ተጠቃሚ እንደሚሆኑ ምክራቸውን ለግሰዋል።

በምስራቅ ጎጃም ዞን አሁን ላይ ከ160 ሺህ በላይ የንብ ቀፎዎች በምርት ስራ ላይ መሆናቸውን ከመምሪያው የተገኘው መረጃ ያመላክታል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.