🔇Unmute
አዲስ አበባ ፤ሕዳር 10/2018 (ኢዜአ)፡- በመንግስት የተያዙ የልማት እቅዶች ግባቸውን እንዲመቱ ሁለንተናዊ ርብርብ ማድረግ እንደሚገባ የከተማ እና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ ገለጹ።
10ኛው የኢትዮጵያ ከተሞች ፎረም "የከተሞች ዕድገት ለኢትዮጵያ ልህቀት" በሚል መሪ ቃል በአፋር ክልል ሰመራ ሎጊያ ሲካሄድ ቆይቷል።
በዛሬው እለትም የፎረሙ የማጠቃለያ መርሀግብር ተካሂዷል።

በመድረኩ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ፣የአፋር ክልል ርእሰ መስተዳድር አወል አርባ፣የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ እንዲሁም ሌሎች ከፍተኛ የመንግስት የስራ ሀላፊዎች ታድመዋል።
የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስትር ጫልቱ ሳኒ በዚሁ ወቅት እንዳሉት፥የኢትዮጵያ ከተሞች በመንግስት የተቀየሰውን የኢትዮጵያ የብልጽግና ጉዞ ለማሳካት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ትልቅ ተልዕኮ ተሰጥቷቸዋል።
የተጀመረውን ፈጣን የብልጽግና ጉዞ በማስቀጠል የዜጎችን ፍትሃዊ ተጠቃሚነት የሚያረጋግጥ ሥርዓት ለመገንባት የሚያስችል የ10 ዓመት መሪ ዕቅድ ላይ ተመስርቶ የተለያዩ ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን ጠቁመዋል።
በሁሉም የልማት መስኮች ውጤት ለማስመዝገብ ከፍተኛ ርብርብ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
እንደ ሀገር ተግባራዊ ለማድረግ የተቀረጹ ሥራዎችን ለማሳለጥ የሚያግዙ በርካታ የሕግ ማዕቀፎች ተቀርፀው ተግባራዊ እየተደረጉ መሆኑን እና ተጨባጭ ለውጦችም መታየት መጀመራቸውን ጠቁመዋል፡፡
በፌደራልና በክልል እንዲሁም በክልል እና በከተሞች መካከል ያለው የዕቅድ መናበብና ቅንጅታዊ አሰራር ከጊዜ ወደ ጊዜ በላቀ ደረጃ መሻሻል እያሳየ መምጣቱን ተናግረዋል፡፡

እነዚህን ሁኔታዎች በቀጣይም ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ገልጸው፥ የብልጽግና ዕቅድ በውጤታማነት ለማጠናቀቅ ከመቼውም በላቀ ሁኔታ መስራት እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡
የከተሞች ፎረም ከተሞችና አጋሮቻቸው የልማትና የመልካም አስተዳደር ሥራዎቻቸውን በማስተዋወቅ እውቅና እንዲያገኙና ተሞክሮዎቻቸውን እንዲለዋወጡ ጉልህ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ተናግረዋል።
እንዲሁም በከተሞች መካከል ጤናማ የውድድር መንፈስ እንዲኖር በማድረግ ለኢትዮጵያ የብልጽግና ጉዞ ትልቅ ፋይዳ ይኖረዋል ብለዋል።
ባለፉት ዘጠኝ ዙሮች እየተካሄደ ባለው የኢትዮጵያ ከተሞች ፎረም ዝግጅቶች ከተሞች በበዓሉ ያላቸው የነቃ ተሳትፎ እያደገ መምጣቱን ጠቁመዋል።
በከተሞች እታየ ያለውን የልማትና የመልካም አስተዳደር መነቃቃት በላቀ ደረጃ ለማስቀጠል ሰፊ የሕዝብ ንቅናቄ ማቀጣጠል እንደሚገባ አመላክተዋል።
ከተሞች ያላቸውን የገቢ አማራጮች በአግባቡ በመለየት መሰብሰብና የከተማውን ህብረተሰብ የልማት ጥያቄ በአግባቡ ለመመለስ መስራት እንዳለባቸው አንስተዋል።
የሕብረተሰቡን ገቢ ለማሻሻል፣ ድህነትን ለመቀነስ እንዲሁም ፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል እንዲፈጠር ለማድረግ ጠንካራ ስራ መስራት እንደሚገባ አመላክተዋል፡፡
በተጨማሪ የከተሞችን የምግብ ዋስትና ችግሮችን በማጥናት እና ለምግብ ዋስትና ችግር ተጋላጭ የሆኑትን የህብረተሰብ ክፍሎች በተለይ ወጣቶች፣ ሴቶች፣ አካል ጉዳተኞች ላይ ትኩረት ማድረግ እንደሚገባ አመላክተዋል፡፡

ሌላው በትኩረት ርብርብ ሊደረግበት የሚገባው የአገልግሎት አሰጣጥ ቀልጣፋነት መሆኑን አንስተዋል።
በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ያለውን እሮሮ ከከተማው ሕብረተሰብ ጋር በመሆን መፍታት እና ቀጣይ መፍትሔ እያስቀመጡ ወደፊት መጓዝ እንደሚገባ አመላክተዋል።
መላው የከተማ ነዋሪ በፖሊሲዎች፣ ስትራቴጂዎች እና ዕቅዶች ዙሪያ የተሟላ ግልጽነት ይዞ ከመንግስት መዋቅር ጋር እንዲሰራ ግንዛቤ መፍጠር እንደሚገባ ጠቁመዋል።
የመሬት አስተዳደር ሥርዓት ኋላቀር ከመሆኑ ጋር ተያይዞ በዘርፉ የተንሰራፋው የመልካም አስተዳደር እጦትና ያልተገባ ጥቅም የመፈለግ አስተሳሰብ መኖሩን ጠቁመዋል።
በቀጣይም የከተሞች ተሞክሮ ተቀምሮ ወደ ሌሎች ከተሞች እንዲስፋፋ እንደሚደረግ አመላክተዋል።
ለፎረሙ ስኬት አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላት ምስጋና አቅርበዋል።
ጅግጅጋ፤ ሚያዝያ 13/2018 (ኢዜአ)፦ በኦዲት ዘርፍ በተከናወኑ የሪፎርም ተግባራት ተጨባጭ ለውጦች እየተመዘገቡ መሆናቸውን የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሠረት ዳምጤ...
Apr 22, 2026
አዲስ አበባ፤ ሚያዝያ 7/2018 (ኢዜአ)፦ኢትዮጵያ በምግብ ዋስትና እና በኢኮኖሚ ልማት ዘርፍ እያከናወነቻቸው ያሉ ተግባራት ለመላው አፍሪካ አገራት ትልቅ አ...
Apr 16, 2026
አዲስ አበባ፤ መጋቢት 24/2018 (ኢዜአ)፦ ሀገራዊ ለውጡ የሀገሪቱን ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ስብራቶች በመጠገን፣ ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ከፍታና ለማህበራዊ ትስስ...
Apr 3, 2026
ቦንጋ ፤የካቲት 16/2017 (ኢዜአ) ፡-በቦንጋ ከተማ የተካሄደውን የህዝብ ውይይት የመሩ ከፍተኛ የመንግስት ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች በከተማው የተለያዩ የልማት ...
Feb 24, 2025