የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ልዩ ዘገባ

<p>ኢትዮጵያ በግብርና፣ በአገልግሎት እና በሌሎች ዘርፎች ቀጣይነት ያለው ዕድገት እያስመዘገበች ነው - የአይ ኤም ኤፍ ማኔጂንግ ዳይሬክተር</p>

Feb 10, 2025

IDOPRESS

አዲስ አበባ፤ የካቲት 02/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ በግብርና፣ በአገልግሎት እና በሌሎች ዘርፎች ቀጣይነት ያለው ዕድገት እያስመዘገበች መሆኑን የዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም ማኔጂንግ ዳይሬክተር ክሪስታሊና ጆርጂዬቫ ገለፁ።

የዓለም አቀፍ የገንዘብ ተቋም (አይ ኤም ኤፍ) ማኔጂንግ ዳይሬክተር ክሪስታሊና ጆርጂዬቫ በኢትዮጵያ የነበራቸውን ቆይታ በተመለከተ ከገንዘብ ሚኒስትሩ አህመድ ሽዴ ጋር በጋራ መግለጫ ሰጥተዋል።

የዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም ቦርድ በሐምሌ ወር 2016 ዓ.ም ለኢትዮጵያ የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ትግበራ በአራት ዓመት የሚከፈል የ 3 ነጥብ 4 ቢሊዬን ዶላር የተራዘመ የብድር አቅርቦት ማጽደቁ ይታወሳል።

ማኔጂንግ ዳይሬክተሯ በመግለጫቸው፤ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና የኢትዮጵያ ህዝብ ላደረገላቸው ደማቅ አቀባበል ምስጋና አቅርበዋል።

በኢትዮጵያ የአጭር ጊዜ ቆይታቸው ውጤታማ ጉብኝት ማድረጋቸውን በመግለጽ፣ የዐድዋ ድል መታሰቢያ የአፍሪካውያን ኩራት መሆኑንም መመልከታቸውን ተናግረዋል።

የኢትዮጵያ የተሟላ የማክሮ ኢኮኖሚ ፖሊሲ ማሻሻያ በመልካም ሂደት ላይ በመሆኑ ውጤት እያስመዘገበ መሆኑንም ገልጸዋል።

የግሉን ዘርፍ በማሳደግ ሰፊ የስራ ዕድል መፈጠሩን መረዳታቸውን ማኔጂንግ ዳይሬክተሯ አስታውቀዋል፡፡

የግብርና እና የአገልግሎት ዘርፉ ቀጣይነት ያለው ዕድገት በማስመዝገብ የዋጋ ግሽበትን በመቀነስ ተጨባጭ ውጤት መመዝገቡን ገልጸዋል።

በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት እያደገ መሆኑን ገልጸው፤ አዲስ አበባ ውብ ከተማ እየሆነች መምጣቷንም መመልከታቸውን ተናግረዋል።

የማክሮ ኢኮኖሚ ሪፎርም ጊዜ የሚጠይቅ በመሆኑ በቁርጠኝነት መስራት እንደሚገባ በማሳሰብ ጊዜው ለኢትዮጵያ ብሩህ ነው ብለዋል።

የገንዘብ ሚኒስትር አህመድ ሽዴ በበኩላቸው፣ አይ ኤም ኤፍ ለሪፎርሙ ውጤታማነት ለሚያደርገው ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል።

መንግሥት አካታች የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ በማድረግ የውጭ ምንዛሪ በገበያ እንዲወሰን አስችሏል ብለዋል።

መንግስት በሞኒተሪንግና ፊሲካል ፖሊሲ ማሻሻያዎች ቀጣይነት ያለው ኢኮኖሚ እድገት ማስመዝገብ መቻሉን ገልጸው፣ የውጭ ምንዛሪ በገበያ እንዲወሰን በመደረጉ በመደበኛና ትይዩ ገበያ መካከል ያለው ልዩነት ጠቧል ብለዋል።

ኢትዮጵያ ለውጭ ኢንቨስተሮች ክፍት መሆኗን ገልጸው፣ የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የአይ ኤም ኤፍ ድጋፍ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ጠይቀዋል።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.