አዲስ አበባ፤ መጋቢት 30/2017(ኢዜአ)፦ ኢትዮጵያ እና የብራዚል የቢዝነስና ኢንቨስትመንት ፎረም ዛሬ በብራዚል ሳኦፖሎ ከተማ መካሄድ ጀምሯል።
በፎረሙ መክፈቻ ላይ በብራዚል የኢትዮጵያ አምባሳደር ልዑልሰገድ ታደሰ፣ የብራዚል የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ዳይሬክተር አንቶኒዮ ሴዛር፣ የኢትዮጵያና ብራዚል የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተወካዮች እና የሁለቱ ሀገራት የንግድ ማህበረሰብ አባላት ተገኝተዋል።
ፎረሙ የኢትዮጵያን እምቅ የኢንቨስትመንት፣ የንግድ እና ቱሪዝም አቅም ማስተዋወቅ ያለመ መሆኑን በብራዚል የኢትዮጵያ ኤምባሲ መረጃ ያመለክታል።
ኢትዮጵያ በንግድ እና ኢንቨስትመንት ያሏት ምቹ እድሎች አስመልክቶ የመነሻ ጽሁፍ ቀርቦ ውይይት ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቃል።
ሁነቱ የኢትዮጵያ እና ብራዚልን የንግድና ኢንቨስትመንት ትብብር የማጠናከር ፋይዳ እንዳለውም ገልጿል።
በፎረሙ ላይ በኢትዮጵያ እና ብራዚል የንግድ ተወካዮች መካከል የአንድ ለአንድ የቢዝነስ ውይይቶች እንደሚደረጉ ኤምባሲው አመልክቷል።
የኢትዮጵያን የኢንቨስትመንት አቅም የሚያስተዋውቅ ፎረም በየካቲት ወር 2017 ዓ.ም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ምስጋኑ አረጋ በተገኙበት በብራዚሊያ መካሄዱ የሚታወስ ነው።