አዲስ አበባ፤ሚያዝያ 4/2017(ኢዜአ)፦በመዲናዋ በ7 ቢሊዮን ብር የኢንዱስትሪ ክላስተር እየተገነባ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባ እና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር አባይ ገለጹ።
የ2017 የአምራች ኢንዱስትሪዎች አውደ ርዕይ ከመጋቢት 29 ጀምሮ "ከሸማችነት ወደ አምራችነት" በሚል መሪ ሐሳብ በአዲስ ዓለም አቀፍ ኮንቬንሽን ማዕከል ተካሄዷል፡፡
ከአውደ ርዕዩ ጎን ለጎን በዘርፉ ያሉ መልካም ተሞክሮዎች እና ተግዳሮቶችን የሚዳስስ ባለድርሻ አካላት የተገኙበት ፓናል ውይይት ትናንት ተካሂዷል።
የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባ እና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ ኃላፊ ጃንጥራር አባይ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፥አስተዳደሩ በአምራች ኢንዱስትሪ ዘርፍ ያሉ ተግዳሮቶችን ለመፍታት በትኩረት እየሰራ ነው።
በዚህም ከተማ አስተዳደሩ በአቃቂ ክፍለ ከተማ በ93 ሄክታር መሬት ላይ የኢንዱስትሪ ክላስተር ልማት ለጥቃቅን እና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች እየሰራ መሆኑን ተናግረዋል።
በ7 ቢሊየን ብር በጀት እየተሰራ ያለው ይህ ክላስተር የገቢያ፣ የኤግዚብሽን እና የውጭ ግብይት ሰንሰለት ያለው ዘመናው የክላስተር ልማት እንደሆነ ገልፀዋል።
ክላስተሩ ሲጠናቀቅ በርካታ ኢንዱስትሪዎች በቀጣይ በሚዘጋጀው የመመልመያ መስፈርት ወደ ክላስተሩ እንደሚገቡ ጠቁመዋል።
በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የአምራች ኢንዱስትሪውን ምርታማነት ለማሳደግ ምቹ ምህዳር እየተፈጠረ መሆኑ ተገልጿል።