አዲስ አበባ፤ ግንቦት 25/2017(ኢዜአ)፦ የገጠር ኮሪደር ልማት ሀገርን የመለወጥ ሰፊ ራዕይ የተሰነቀበት ሀገራዊ ውጥን ነው ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) ገለጹ።
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከንባታ ዞን አዲሎ ዙሪያ ወረዳ ሀሚዶ ቀበሌ የገጠር ኮሪደር ልማትን አስጀምረናል ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባስተላለፉት መልዕክት።
በተጨማሪም በቀበሌው የሚኖረው አንድ የአርሶ አደር ሞዴል የገጠር መንደርን መጎብኘታቸውን ጠቁመው አርሶ አደሩ ጽዱ፣ ጤናማና ለማየት እጅግ ማራኪ የሆነ የመኖሪያ አካባቢን በመኖሪያ ግቢው ውስጥ በመፍጠር ምሳሌ የሚሆን ስራ አከናውኗል ብለዋል።
ጽዱ የመኖሪያ ስፍራን ከመፍጠር ባለፈ በሌማት ትሩፋትና በጓሮ አትክልት ልማት ላይም ንቁ ተሳተፎ እያድረገ ይገኛል ነው ያሉት በመልዕክታቸው።
ይህ ስራ በሁሉም አካባቢ በትብብር ሊሰፋ ይገባል ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ።
እንዲሁም በዞኑ ልዩ የተፈጥሮ ገጸ በረከት የሆነው ሀምበርቾ ተራራን በማህበረሰብ ተሳትፎ የኢኮ ቱሪዝም ማዕከል ለማድረግ የተከናወኑ ስራዎችም እጅግ የሚደነቁ ናቸው ብለዋል።
በተራራው የተገነባው 777 የመወጣጫ ደረጃ አካባቢውን ተደራሽ የመስህብ ስፍራ ያደርገው ሲሆን፣ ተራራ መውጣትና የተለያዩ የአእዋፋት ዝርያዎችን መመልከት የሚወዱ ቱሪስቶች ወደ እዚህ ስፍራ በመምጣት ማራኪ ጊዜን ማሳለፍ ይችላሉ ነው ያሉት።