🔇Unmute
ገንዳ ውሃ/ ሰቆጣ ፤ ጥቅምት 1/2018 (ኢዜአ)፡- በባሕር በር ጉዳይ የመንግስት አቋምና የዲፕሎማሲ ጥረቱ እንዲሳካ ሁላችንም የድርሻችንን ለመወጣት ዝግጁ ነን ሲሉ በአማራ ክልል ኢዜአ ያነጋገራቸው የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ገለጹ።
የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አፅቀሥላሴ መስከረም 26 ቀን 2018 ዓ.ም በሕዝብ ተወካዮችና የፌዴራሽን ምክር ቤቶችየጋራ ስብሰባ የመክፈቻ ንግግር ባደረጉበት ወቅት የመንግስትን የትኩረት አቅጣጫዎች አመላክተዋል።
በፕሬዝዳንቱ ከተነሱት ዋና ዋና ነጥቦች መካከል የባሕር በር ጥያቄ እና የመንግስትን የዲፕሎማሲ ጥረትና ነባራዊ ሁኔታውን አንስተዋል።
ኢትዮጵያ የባሕር በር ጥያቄ ተገቢና ፍትኀዊ በመሆኑ አስተማማኝ እና ዘላቂ የባሕር በር የማግኘት ጥረቱ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍ ወዳለ ደረጃ ላይ ደርሷል ብለዋል።
በዚሁ ጉዳይ ላይ ፕሬዝዳንቱ ያደረጉትን ንግግር ተከትሎ የኢዜአ ሪፖርተር በአማራ ክልል የተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችን አነጋግሯል።
የባሕር በር ጥያቄ ለኢትዮጵያውያን የሕልውና ጉዳይ መሆኑን መንግስት ጽኑ አቋም ይዞ የዲፕሎማሲ ጥረቱን አጠናክሮ መቀጠሉን ጠቅሰው ለስኬቱ ሁላችንም የድርሻችንን ለመወጣት ዝግጁ ነን ብለዋል።
በምዕራብ ጎንደር ዞን የመንግስት ሰራተኛ የሆኑት ብሩክ ወርቄ፤ የኢትዮጵያ የባሕር በር መሻት የቅንጦት ሳይሆን የህልውና ጉዳይ በመሆኑ ለመኖር ስንል የምናሳካው መሆን አለበት ሲሉ አንስተዋል።
በዞኑ ገንዳ ውኃ ከተማ የሚኖሩት ሃምሳ አለቃ ተመቸ ጎሹ፤ ኢትዮጵያ የባሕር በር ማጣት ሳይኖርባት ለረጅም አመታት የባህር መውጫና መግቢያ የተቆለፈባት መሆኑ ሁላችንንም ያስቆጨ ነው ብለዋል።
በመሆኑም አሁን ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) እና መንግስታቸው ኢትዮጵያ ያለ ባህር በር መኖር እንደማትችል ለዓለም በማስረዳት ምላሽ እንድታገኝ የጀመሩትን የዲፕሎማሲ ጥረት አድንቀዋል።
በዚህም መሰረት ጥያቄው በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍ ወዳለ ደረጃ መድረሱን ፕሬዝዳንቱ በንግግራቸው ያነሱት መሆኑን አስታውሰው የመንግስት ጥረት እንዳለ ሆኖ የሁላችንም እገዛና ትብብር ያስፈልጋል ብለዋል።
በዋግኸምራ ብሔረሰብ አስተዳደር የሰቆጣ ከተማ ነዋሪ አቶ ሃይሉ ደርበው፤ መንግስት የሃገራችን የባህርበር ጥያቄ በሰላማዊና ህጋዊ በሆነ መንገድ ለመመለስ እየሰራ ያለው ተግባር የሚደነቅ ነው ብለዋል።
የኢትዮጵያዊያን የህልውና ጉዳይ የሆነውን የባህር በር ጥያቄ ምላሽ እንዲያገኝ ሁላችንም በአንድነት በመቆም ልንደግፈው ይገባል ሲሉ ገልጸዋል።
ሌላው የከተማው ነዋሪ አቶ ሹመት ተስፋዬ በበኩላቸው ፤ጥያቄው በሰላማዊና በህጋዊ መልኩ እንዲመለስ መንግስት የሰጠው ትኩረትና ያሳየውን ቁርጠኝነት በመደገፍ ለውጤታማነቱ የበኩላቸውን እንደሚወጡ ተናግረዋል።
ፍትሃዊ የሆነው የኢትዮጵያዊያን የባህር በር ጥያቄ ምላሽ እንዲያገኝ በመንግስት ዋና አጀንዳ መደረጉ የሚደገፍ ነው ነው ያሉት ደግሞ ወይዘሮ መሰረት ካሳሁን ናቸው።
የኢትዮጵያን የባሕር በር ጥያቄ በተመለከተ ህዝቡ በድጋፍ ሰልፍ ጭምር እውቅና የሰጠው መሆኑን ያስታወሱት አስተያየት ሰጪዎቹ ፤ በሁሉም ረገድ ድጋፍና ትብብራችን ተጠናክሮ ይቀጥላል ሲሉ አረጋግጠዋል።
Jul 17, 2025
Apr 24, 2025
አዲስ አበባ፤የካቲት 4/2017(ኢዜአ)፦ የሲሚንቶ ንግድ እና መሰረታዊ የፍጆታ እቃዎችን በተመለከተ የወጡ መመሪያዎች ገበያውን በማረጋጋትና የዋጋ ግሽበትን በመቀ...
Feb 12, 2025