የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ
ግንኙነት
ፈልግ
ልዩ ዘገባ

የአፍሪካ ህብረት ያዘጋጀው የመጀመሪያው የዲጂታል ግብርና ኮንፍረንስ ዛሬ በአዲስ አበባ ይጀመራል

Dec 2, 2025

IDOPRESS

🔇Unmute

አዲስ አበባ፤ ህዳር 22/2018(ኢዜአ)፦ የአፍሪካ ህብረት ያዘጋጀው የመጀመሪያው የዲጂታል ግብርና ኮንፍረንስ በህብረቱ ዋና መቀመጫ አዲስ አበባ ከዛሬ ጀምሮ ይካሄዳል።


“ኢኖቬሽን እና የዲጂታል መፍትሄዎችን ጠንካራ፣ አረንጓዴ እና በቴክኖሎጂ የታገዘ የግብርና ዘርፍ ግንባታ በመጠቀም የአፍሪካን መጻኢ ጊዜ ብሩህ ማድረግ” የኮንፍረንሱ መሪ ሀሳብ ነው።


የግብርና ምርታማነትን ማሳደግ፣ የዲጂታል ግብርና ኤክስቴሽን አገልግሎት፣ የግብርና ቴክኖሎጂ እና ኢኖቬሽን፣ የገበያ ተደራሽነት፣ የእሴት ሰንሰለትን ማጠናከር፣ የግብርና ምርታማነትን ከአየር ንብረት ለውጥ የማይበገር አቅም መገንባት ጋር ያስተሳሰረ አካሄድን መከተል፣ የግብርና ፖሊሲዎችና የህግ ማዕቀፎች ትግበራ በኮንፍረንሱ የሚመከሩባቸው አጀንዳዎች ናቸው።


ኮንፍረንሱ የእውቀት ሽግግር እና ፖሊሲ ተኮር ውይይቶች የሚደረግበት ሲሆን ስኬታማ የሀገራት የግብርና ኢኒሼቲቮች ለተሳታፊዎች ይቀርቡበታል።


በአፍሪካ የዲጂታል ግብርና መፍትሄዎችን ተደራሽነት የሚደግፉ ስትራቴጂዎች የመለየት እና አጋርነቶችን ማጠናከር ከሁነቱ የሚጠበቅ አበይት ውጤት መሆኑን ኢዜአ ከአፍሪካ ህብረት ያገኘው መረጃ ያመለክታል።


ኮንፍረንሱ የአፍሪካ ህብረት እ.አ.አ 2024 ያፀደቀውን አህጉራዊ የዲጂታል ግብርና ስትራቴጂ ተፈጻሚነት የማሳደግ ጥረት አካል መሆኑንም አመልክቷል።


የግብርና ስትራቴጂው ከአጀንዳ 2063 እና ከረጅም ጊዜ የአፍሪካ የልማት እቅድ ጋር የተጣጣመ መሆኑን ነው ህብረቱ የገለጸው።


ስትራቴጂው ኢንፎርሜሽንና ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ(አይሲቲ) በመጠቀም አህጉራዊ የዲጂታል ገበያ መገንባት እና ግብርናን ከአፍሪካ የዲጂታልና ዘላቂ ልማት ግቦች ጋር የማስተሳሰር ግብ ያለው ነው።


እስከ ሕዳር 24 ቀን 2018 ዓ.ም በሚቆየው በዚህ መድረክ የአፍሪካ ሀገራት ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣናት እና ፖሊሲ አውጪዎች፣ የግብርና ተመራማሪዎች እና ሳይንቲስቶች፣ የቴክኖሎጂ ባለሙያዎች፣ አርሶ አደሮች እና የአርሶ አደር ተቋማት፣ የምርምር ተቋማት፣ባለሀብቶች፣ የልማት አጋሮች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ይሳተፋሉ።

የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት - የኢትዮጵያ ድምጽ

የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ወቅታዊ፣ ትክክለኛ እና አጠቃላይ የዜና ዘገባዎችን ለማቅረብ የሚሰራ የኢትዮጵያ የዜና ወኪል ነው። ጠቃሚ የሀገር ውስጥ እና አለምአቀፍ ሁነቶችን እንዘግባለን፣ ሀገራዊ ፖሊሲዎችን እና ማህበራዊ ለውጦችን በጥልቀት በመመርመር ለህዝብ፣ ለመንግስት ኤጀንሲዎች፣ ለንግድ ድርጅቶች እና ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ታማኝ የዜና ምንጭ እናቀርባለን። ጋዜጠኞቻችን በአገር ውስጥ እና በውጭ አገር አዳዲስ ዜናዎች እና መረጃዎች በተቻለ ፍጥነት እንዲደርሱ እና ግልጽነትን እና የህዝብ ተሳትፎን ለማስተዋወቅ ነው.